የዓይነ ስውራን ትምህርት በኢትዮጵያ
ዓርብ፣ ነሐሴ 22 2007የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ማንኛውም ሰው የመማር መብት እንዳለው ይደነግጋል። ይሁንና ይህ መብት በተለይ በአዳጊ ሀገራት በተለያዩ ምክንያቶች ሳይከበር ይስተዋላል። ከነዚህ ምክንያቶች አንዱ ትምህርት ቤት የማግኘት እድል ነው። በተለይ ደግሞ አካለ ጉዳተኛ ሲሆን ፤ ፈተናው ይበልጥ ይከፋል።
አለውያ በመርሃ እውራን ትምህርት ቤት የመማር እድል ካገኙ ኢትዮጵያውያን ዓይነ ስውራን አንዷ ናት። ዛሬ የ2ኛ ዓመት የህግ ተማሪ የሆነችው አለውያ በወቅቱ ትማርበት የነበረው መርሃ እውራን አዳሪ ትምህርት ቤት ለመግባት ኦሮሞ መሆኔና ፤ሰው ማወቄ ጠቅሞኛል ትላለች።በትምህርት ቤቱ ሁሉም ዓይነ ስውራን እኩል የመማር እድል ማግኘት አለመቻላቸው ብቻ ሳይሆን ፤ ጭራሽ ትምህርት ቤቱ በሚመጣው ዓመት ዓይነ ስውራን ተማሪዎቹን ስለመቀበሉ ስጋት እንዳለ ዶይቸ ቬለ ከተማሪዎች ጥቆማ ደርሶታል። እንዲሁ የዚሁ ዓይነ ስውራን ትምህርት ቤት ተማሪ የነበረው አበራ፤ የዓይነ ስውራን ተማሪዎች ስጋት ከጀመረ ቆየ ይላል።
አቶ ሱልጣን ይስሙ፤ የኢትዮጵያ ዓይነ ስውራን ብሔራዊ ማህበር ዋና ስራ አስኪያጅ ናቸው። በሰበታ መርሃ እውራን ትምህርት ቤት ተምረዋል፤ እንዲሁም ለ7 ዓመታት ያህል በመምህርነት አገልግለዋል። አቶ ሱልጣን ግን በቅርበት የሚያውቁት ትምህርት ቤት የመዘጋት ጉዳይ ትክክለኛ መረጃ አይደለም ይላሉ።
አቶ ፍቃዱ ፀጋ የኢትዮጵያ ዓይነ ስውራን ብሔራዊ መሀበር የስራ ቦርድ ሰብሳቢ ናቸው። እሳቸው ተማሪ በነበሩበት ጊዜ የዓይነ ስውራን የመማሪያ መገልገያዎች እጥረት ብቻ ሳይሆን እነሱን ተቀብለው የሚያስተምሩ የከፍተኛ ተቋም እጥረትም ኢትዮጵያ ውስጥ ነበር። ምንም እንኳን የተማሪው እና ትምህርት የሚሰጡት የከፍተኛ ተቋማት ቁጥር ቀስ በቀስ ቢጨምርም፤ የመማር እድል የሚያገኙ ዓይነ ስውራን ወይም አካል ጉዳተኛ ቁጥር ግን አቶ ፍቃዱ እንደሚያስረዱት አሁንም ትንሽ ነው።
ኢትዮጵያ ውስጥ ጥያቄ ስላስነሳው የሰበታ መርሃ እውራን ትምህርት ቤት እና በአጠቃላይ ዓይነ ስውራን በኢትዮጵያ ስለሚያገኙት የትምህርት እድል፤ ከድምፅ ዘገባው ያገኛሉ።
ልደት አበበ
ሸዋዬ ለገሰ