የኮንጎ ዜጎች ከማያዉቁት ጠላት የተደቀነባቸው ስጋት
ሐሙስ፣ ታኅሣሥ 2 2007
በሌላ በኩል ፕሬዚዳንት ጆሴፍ ካቢላ ተቃዋሚዎችን በማካተት ካቢኔያቸዉን በአዲስ ማዋቀራቸዉን አስታዉቀዋል።
የሰሜን ምሥራቃዊ ኮንጎ ከተማ ቤኒ ከተማ በተደጋጋሚ እየደረሰ ባለዉ አሰቃቂ ጭፍጨፋ ምክንያት ሰላምን ካጣች ወራቶች ተቆጠሩ። ካለፈዉ ሳምንት ቅዳሜ እስከ አሳለፍነዉ ሰኞ ድረስ 50 ሰዎች የዚህ ግድያ ሰለባ ሆነዋል። አህሊ በተሰኘዉ ገጠር የሚገኙ አይን እማኞች እንደገለፁት ፣ የወንጀል ፈፃሚዎቹ ተግባር ጭካኔ የተሞላበት ነው።
« አጥቂዎቹ መጀመርያ ሰዎችን ይገድላሉ። ከማምለጣቸዉ በፊት ደግሞ ገጠሩን በእሳት ያያይዛሉ። ከአደጋዉ የተረፉ የገጠሪቱ ነዋሪዎችም የግድያ እጣ እንዳይcጥማቸው በመስጋት ቦታዉን ለቀዉ ይሄዳሉ። በመሆኑም አካባቢው ባዶዉን ይቀራል። እኔ ራሴ ነገ ምን ሊከሰት እንደሚችል አላዉቅም። »
በሀገሪቱ የሚታየዉ ጭካኔ የተሞላበት ጭፍጨፋ እጅግ መደንገጣቸዉን የገለፁት በሰሜናዊ ኪቩ ግዛት የሚገኙ የሲቭል ማሕበረሰብ ድርጅቶች የፊታችን እሁድ ለሁለት ቀናት የሚዘልቅ የሐዘን ጥሪ አቅርበዋል። ይህ ጥሪ ስለሚካሄደው ግድያ እና ሽብርተኝነት ተግባር ዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ እንድያዉቀዉና እንድያጤነዉ ለማድረግ የታሰበ መሆኑም ተገልፆአል።
በዴሞክራቲክ ኮንጎ የተሰማራው የተመድ ተልዕኮ በምሕፃሩ «MONUSCO» ከኮንጎ ወታደራዊ ኃይል ጋር በመተባበር ወንጀል ፈፃሚዎቹን አማፅያንን ለማጥቃት ጥሪ አስተላልፎአል፤
የ MONUSCO-ኃላፊ ጀርመናዊዉ ማርቲን ኮብለር በኮንጎ የሚታየዉን ጭካኔ የተሞላበት ወንጀል አዉግዘዋል። ከጥቅምት ወር ጀምሮ ቤኒ በተሰኘዉ በሰሜናዊ ዴሞክራቲክ ኮንጎ ገጠር እየታየ ያለዉ ድንገተኛ ጭፍጨፋ እስካሁን 250 ሰዎች ተገድለዋል። እስካሁን ግን ይህን ወንጀል እየፈፀመ ያለዉ ማንነት በግልፅ አልታወቀም። እንደ አብዛኛ ነዋሪዎች ጥርጣሪ ግን ዩጋንዳን ነፃ ለማድረግ የዴሞክራቲ ጥምር ብሔራዊ ጦር በምህፃሩ ADF-NALU በሚል የሚታወቀዉ እስላማዊ አማፂ ቡድን ሳይሆን አልቀረም። ይህ የአማፂ ቡድን የዩጋንዳን ፕሬዚዳንት ዩዎሪ ሙሴቪኒ በመቃወም ጦርነት እንዳወጀ፤ በጎርጎርጎረሳዉያኑ 1995 ዓ,ም በምስራቃዊ ኮንጎ ላይ መስፈሩ ይታወቃል። እንደ አንዳንድ ምሁራን ከሆነ ደግሞ፤ ይህ ቡድን ቆየት ብሎ እስላማዊ ፅንፈኝነትን እንደያዘና እንደ ሶማልያዉ የአሸባብ ቡድን ከፅንፈኛ ቡድኖች ጋር በጋራ ሳይሰራ አይቀርም ሲሉ ጥርጣሪያቸዉን ይገልፃሉ። በአጠቃላይ በምሥራቅ ኮንጎ ከADF-NALU ጎን ሌሎች እስከ 50 የሚደርሱ በርካታ አማፅያን ቡድኖች መኖራቸው እና በየበኩላቸው የግድያ ተግባር ሊፈፅሙ ስለሚችሉ በአንፃራቸው ርምጃ ሊወሰድ እንደሚገባ ነው የ MONUSCO ኃላፊ ማርቲን ኮብለር የገለጹት።
«ሌሎቹም ማለት ሚይ ሜይ የሚባሉት ቡድኖችንም መዋጋት ያስፈልጋል። ADF የተባለዉን አማፂ ቡድን ተዋግተን አዳክመነዋል። ሌሎች ስብጥርጣሪ ቡድኖችም አሉ፤ ከነዚህ ቡድኖች መካከል ደግሞ ይንን ጭካኔ የተሞላበት አረመኒያዊ ድርጊት ሊፈፀም ይችላል። ከዴሞክራቲክ ኮንጎ የጦር ኃይል ጋር በጋራ በመሆን ይህን ድርጊት ለማስቆም መወሰን ይኖርብናል።»
በሌላ በኩል የሀገሪቱ ፕሬዚዳንት ጆሴፍ ካቢላ ሰሞኑን ካቢኔያቸዉን በአዲስ ማዋቀራቸዉን አስታዉቀዋል። ካቢላ የብሔራዊ አንድነት መንግሥት ለመመስረት ባለፈዉ ዓመት ቃል በገቡት መሰረት አንዳንድ የሚንስትርነትን ሥልጣን ለተቃዋሞዎቻቸዉ ሰጥተዋል። ይህ ፖለቲካዊ ስምምነት ሰዓቱን ጠብቆ የመጣዉ የሃገሪቱ መሪ ሕገ-መንግሥቱን ቀይረዉ ለጎርጎረሳዉያኑ 2016 ዓ,ም ለሶስተኛ የስልጣን ዘመን መዘጋጀት በያዙበት ጊዜ ነው።
የኮንጎ መንግሥት ተቃዋሚ ግን በካቢላ አዲስ የካቢኔ ምሥረታ እንብዛም አልተገረመሙም። የኮንጎ ነፃነት ንቅናቄ በአህፅሮቱ የ «MLC» ዋና ፀሃፊ እና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ቶማስ ሉካ ስልጣኑን ባገኙ በዝያዉ ምሽት ከፓርቲያቸዉ መወገዳቸዉ ታዉቋዋል።
ፊሊፕ ሳንደር /አዜብ ታደሰ
አርያም ተክሌ