የክርስቲያኖች በጎ ተግባር በረመዳን
ረቡዕ፣ ሐምሌ 17 2005ከናይጀሪያ ዋና ከተማ አቡጃ በስተሰሜን የምትገኘው ትልቋ ከተማ ካዱና ባለፉት 10 ዓመታት በክርስቲያኖችና ሙስሊሞች መካከል የሚካሄድ ደም አፋሳሽ ግጭት ተምሳሌት ሆና የምትታይ ከተማ ነበረች ። በወቅቱ ሁለቱም ሃይማኖቶች ተፅእኖ ለማድረግና የበላይነትን ለመያዝ ባካሄዱት ትግል በሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ህይወት ጠፍቷል ። አሁን ግን ሁኔታዎች ተለውጠዋል ። በዘንድሮው ረመዳን እንኳን አንድ የአካባቢው ቄስና በጎ ፈቃደኞች ሙስሊም እስረኞች የረመዳንን ወር በቤታቸው እንዲያሳልፉ ዋስ ሆነው አስለቅቀዋቸዋል ።
ቄስ ዮሃና ቡሮ ና አንድ የበጎ ፈቃደኖች ቡድን ከሰሜን ናይጀሪያዋ ከተማ ካዱና 30 ሙስሊም ወንድ ና ሴት እስረኞችን ነበር የገንዘብ ቅጣታቸውን በመክፈልና ዋስ በመሆን ያስለቀቁት ። ይህን ያደረጉትም እስረኖቹ ረመዳንን ከቤተሰቦቻቸው ጋር እንዲፆሙ በማሰብ ነው ። በካዱና ፌደራል ክፍለ ሃገር እሥር ቤት ውስጥ የተያዙት እነዚህ እስረኞች የተጣለባቸውን የገንዘብ ቅጣት ወይም በዋስትና ማስያዝ የሚገባቸውን ገንዘብ መክፈል ባለመቻላቸው ነበር የታሰሩት ።
እና አሁን የወንጌላውያን ቤተ ክርስቲያን ሃላፊ ቄስ ዮሃናና ከ 30 በላይ የሚሆኑ የመሰል አብያተ ክርስቲያን ባልደረቦች የገንዘብ ቅጣቱን እና መከፈል የነበረበትን የዋስ ገንዘብ ብቻ ሳይሆን እሥረኞቹ ለጉዞ የሚያስፈልጋቸውን ወጪም ሸፍነዋል ። በቄስ ዮሃና እምነት ፀሎትና ፆም ለሠላም አስተዋፅኦ አለው ።
« የረመዳን ፆም ከአምስቱ አበይት የእስልምና መሠረቶች አንዱ ነው ። በዚህ የጾም ወቅት እኛ ክርስቲያኖች በችግር ላይ ያሉ ሙስሊሞችን ስንረዳ እንደሰታለን ። ሙስሊም ወንድሞቻችን መፆምና በሃገራቸው ሠላም እንዲሰፍንም መፀለይ እንዲችሉ ይለቀቁ ዘንድ ጥረት አድርጌያለሁ ። በቁርዓንም ይሁን በመፀሐፍ ቅዱስ የተጠቀሰውን ሃያማኖታዊ ግዴታችንን መወጣት ይገባናል ።»
ቄስ ቡሮና ሌሎችም ክርስቲያኖች ናይጀሪያ ውስጥ በሁለቱ ሃይማኖቶች መካከል የተሻለ የሰመረ ግንኙነት እንዲኖር ይፈልጋሉ ። ይሁንና እውነታው የተለየ ነው ። ከአፍሪቃ በህዝብ ብዛት አንደኛ ደረጃ ላይ በምትገኘው በናይጀሪያ በክርስቲያኖችና በሙስሊሞች እንዲሁም በተለያዩ ጎሳዎች መካከል ግጭቶች ይከሰታሉ ። ከሁለቱም ወገኖች ሰዎች ይሞታሉ ። አብያተ ክርስቲያንም ሆነ መስጊዶች ይቃጠላሉ ። እነዚህን የመሳሰሉ አሳዛኝ ድርጊቶች በሚፈፀሙባት በናይጀሪያ ቄስ ቡሮና ሌሎች ደጋፊዎቻቸው ያከናወኑት በጎ ተግባር ሙስሊም የሃይማኖት አባቶችንና የካዱና ነዋሪዎችንም አስደስቷል አስደምሟልም ። ሼክ ሳሊሁ ማይ ባሮታ የካዱና ነዋሪ ሙስሊም የሃይማኖት አባት ናቸው ። ለተለቀቁት ሙስሊሞች ባሰሙት ንግግር እንዳሉት በጎው ተግባር ለሁሉም አርአያ ሊሆን ይገባዋል ።
«ቄስ ቡሮ ያከናወኑት ተግባር ለሁላችንም በተለይ በሰላም አብሮ ስለመኖር በራድዮ ለሚናገሩ ባለሥልጣናትና የሃይማኖት መሪዎች ምሳሌ መሆን አለበት ። ዛሬ ሙስሊሞች እንዲለቀቁ ያበቃው አንድ ክርስቲያን ቄስ መሆኑ ሁላችሁንም ሳያስገርማችሁ አይቀርም ።»
ማርያም አቡበከር በሙስሊሞችና በክርስቲያኖች መካከል ሰላምና መግባባት እንዲሰፍን የሚጥረው የሴቶች ድርጅት ሃላፊ ናቸው ። የቄስ ቡሮ ተግባር ሌሎችንም እንደሚያነሳሳ ጥርጥር የላቸውም። ከዚህ ውጭ ግን የናይጀሪያ ወህኒ ቤቶች ይዞታ በእጅጉ ያሳስባቸዋል ።
« እስረኞች የተፈረደባቸውን ጊዜ በእሥር ቤቶች ውስጥ የሚያሳልፉበት ሁኔታ በጣም ያሳዝነኛል ። ስለዚህ ሁሉም ክርስቲያኖችም ሙስሊሞችም በተቻላቸው መጠን እስረኞችን እንዲረዱ ጥሬ አቀርባለሁ ።»
ነፃ የወጡት እስረኞችም የእስር ቤቱ ይዞታ አስከፊ መሆኑን ነው የተናገሩት ።
« ፍየል ገጭቼ የተፈረደብኝን 1000 ናይራ ወደ 50 ዩሮ በአንድ ወር ውስጥ መክፈል ባለመቻሌ ነው የታሰርኩት ። 240 ቀናት መቆየት አለብኝ ። እዚህ አያያዛቸው ሰብዓዊነት ይጎድለዋል ።»
« ማንም ፣ ጠላቴም ቢሆን እዚህ እንዲመጣ አልመኝም ፤ በእውነት እዚህ ቤት ውስጥ መሆን ጥሩ አይደለም ። »
የካዱና እሥር ቤት ጠባቂዎችም እሥረኞቹ ያሉት እውነት መሆኑን አረጋግጠዋል ። በዚህ አጋጣሚም ባለሃብቶች መንግሥትና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ለአሥረኞች ምግብ ልብስና ንፅህን መጠበቂያ በመለገስ እንዲታደጓቸው ጥሬ አስተላልፈዋል ።
ኢብራሂማ ያኩባ
ሂሩት መለሰ
አርያም ተክሌ