የኬንያ ተቃዋሚ ጥምረት እና አይ ሲ ሲ
ረቡዕ፣ ጥቅምት 20 2006
ጥረቱ የከሸፈው «ኮዋሊሽን ፎር ሪፎርምስ ኤንድ ዴሞክራሲ» በሚል መጠሪያ የሚታወቀው ዋነኛው የተቃዋሚው ጥምረት ትናንት አባላቱ የሆኑ ሀገረ ገዢዎች፣ እንዲሁም፣ የብሔራዊ እና ያካባቢያዊ ምክር ቤት ቡድኖች ካካሄዱት ምክክር በኋላ በኬንያውያኑ መሪዎች ላይ በዘ ሄግ ኔዘርላንድስ የተጀመረው የችሎት ሂደት መቀጠል አለበት በሚል አቋሙ በመፅናቱ ምክንያት መሆኑ ተገልጾዋል።
በኬንያ ምክር ቤት የሚወከሉት የተለያዩት ፓርቲዎች እንደራሴዎች የሀገሪቱ ፕሬዚደንት እና ምክትላቸው ችሎት ወደሌላ ጊዜ ይተላለፍ የሚለውን ሀሳብ ያነቃቁት በሀገሪቱ የአንድነቱን ስሜት ለመፍጠር በማሰብ ነበር። ይሁን እንጂ፣ የተቃዋሚዎች ጥምረት «ኮዋሊሽን ፎር ሪፎርምስ ኤንድ ዴሞክራሲ» ትናንት የአምስት ሰዓት ምክክር ካደረገ በኋላ ፣ በኬንያውያኑ ባለሥልጣናት ላይ የዓለም አቀፉ የጦር ወንጀለኞች መዳኛ ፍርድ ቤት ፣ አይ ሲ ሲ የመሠረተው የክስ ሂደት መቀጠል አለበት በሚል ይዞት በቆየው አቋሙ መፅናቱን የቡድኑ የሕግ ጉዳዮች ተጠሪ ጄምስ ኦሬንጎ አስታውቀዋል።
«አይሲሲን በተመለከተ አቋማችን ግልጽ ነው፣ አልተቀየረም፣ አፅንዖት መስጠት የፈለግነው ነገር ችሎቱ እዚያው ዘ ሄግ መቀጠል እንዳለበት ነው። ገዢው የጁብሊ ፓርቲ ሁኔታውን መለወጥ ከፈለገ፣ ከሮሙ ስምምነት ሙሉ በሙሉ መውጣት አለበት። ከዚህ ውጭ በየትኛውም የተመድ ደንብም ሆነ ሕግ አባል መንግሥታት የክሱን ሂደት ማራዘም አይችሉም። »
ይሁንና፣ እአአ በ2005 ዓም ከተካሄደው ፕሬዚደንታዊ ምርጫ በኋላ በተፈጠረው ግጭት የተጎዱት ሰለባዎች ፍትሕ ማግኘት ይችሉ ዘንድ በዚሁ ጥያቄ ላይ ከመንግሥት እና ከዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ጋ በዚያው በሮሙ ስምምነት ማዕቀፍ ገንቢ ውይይት ለማድረግ ዝግጁ መሆኑን ፓርቲው አመልክቶዋል።
የትናንቱን ምክክር የተከታተሉት የፖለቲካ ተንታኝ ባሮን ሺቲሚ እንዳስረዱት፣ የተቃዋሚው ጥምረት ገዢው ፓርቲ ሀገሩን ከአይሲሲ ለማስወጣት የያዘውን ዕቅድ ይተዋል የሚል ተስፋ አሳድሮዋል።
« የዛሬው ስብሰባ ገዢው ፓርቲ ይህን ረቂቅ ሀሳብ ለምክር ቤት ካቀረበ የተቃዋሚው ወገን እንደሚቃወመው መልዕክት ያስተላለፈ ነበር። ለፖለቲካ ጥቅም ነው መባሉ ትክክለኛ አይደለም። በዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት በወንጀል የተከሰሰ ፕሬዚደንት መኖሩ ጥሩ አይደለም፣ ግን፣ ለኛ ለኬንያውያን ፍርድ ቤቱ ለሀገር ስም እና ክብር በጣም ጥሩ ነው። »
የተቃዋሚው ጥምረት ከትናንቱ ስብሰባው በኃላ በፕሬዚደንቱ እና በምክትላቸው ላይ የተመሠረተውን ክስ በተመለከተ አቋሙን ይቀይራል በሚል ተስፋ ተደርጎ ነበር። የፕሬዚደንት ኬንያታ ችሎት እአአ የፊታችን ህዳር 12 በዘ ሄግ፣ ኔዘርላንድስ ይጀመራል።
አርያም ተክሌ
ነጋሽ መሀመድ