የኬንያ ምርጫና እክሉ
ረቡዕ፣ የካቲት 27 2005
ኬንያ ዉስጥ ባለፈዉ ሰኞ በተደረገዉ ምርጫ ምክትል ጠቅላይ ሚንስትር ኡሑሩ ኬንያታ ተቀናቃኞቻቸዉን እየመሩ ነዉ።እስካሁን ከተቆጠረዉ ፥ኬንያታ ሐምሳ ሰወስት ከመቶዉን ድምፅ ሲያገኙ ዋነኛ ተቀናቃኛቸዉ ራይላ ኦዲንጋ በአርባ ሁለት ከመቶ ድምፅ ይከተላሉ።ዛሬ የድምፅ መቆጠሪያዉ የኮሚፒዉተር ሥርዓት መዛባቱ ግን ጥርጥሬንና ዉዝግብን አስከትሏል።የአዉሮጳ ሕብረት የታዛቢዎች ቡድን የድምፅ አሰጣጡን ሒደት አድንቋል፥ የኬንያታ ፓርቲ በበኩሉ ብሪታንያ በምርጫዉ ሒደት ጣልቃ ገብታለች በማለት የቀድሞዋን የኬንያ ቅኝ ገዢ ተቃዉሟል።ነጋሽ መሐመድ አጭር ዘገባ አለዉ።
ገለልተኛዉ ብሔራዊ ምርጫ ኮሚሽን ዛሬ እንዳስታወቀዉ ከአጠቃላዩ ድምፅ አርባ ከመቶዉ ተቆጥሯል።በተለይ ለፕሬዝዳትነት ከተቆጠረዉ ድምፅ ኡሑሩ ኬንያታ በሐምሳ-ሰወስት ከመቶ አንደኛ፥ ራይላ ኦዲንጋ በአርባ ሁለት ከመቶ ድምፅ ሁለተኛዉን ሥፍራ ይዘዋል።
ያሁኑ ምክትል ጠቅላይ ሚንስትር ኡሑሩ ኬንያታ የኬንያ የመጀመሪያ ፕሬዝዳት የጆሞ ኬንያታ ልጅ፥ ያሁኑ ጠቅላይ ሚንስትር ራይላ ኦዲንጋ ደግሞ የመጀመሪያዉ የኬንያ ምክትል ፕሬዝዳት የጃራሚጊ ኦዲንጋ ኦዲንጋ ልጅ ናቸዉ።
የድምፅ አሠጣቱን ሒደትና የመራጩን ትዕግሥት፥-የአዉሮጳ ሕብረት የታዛቢዎች ቡድን መሪ የቀድሞዉ የስሎቬንያ ጠቅላይ ሚንስትር አልዮስ ፔተርለ እንዳሉት ሲበዛ አስደናቂ ነዉ።
«ባለፈዉ ሰኞ ኬንያዉያን ለሠላምና ለመብታቸዉ መከበር በፅናት ቆመዋል።መብታቸዉን ለማስከበር ያሳዩት ፅናት ለአካባቢዉ ሐገራት ብቻ ሳይሆን ለመላዉ ዓለምም ጥሩ ምሳሌ ነዉ።ለትዕግሥት የኖቤል ሽልማት ቢሰጥ ኖሮ ኬንያዎች ባለፈዉ ሰኞ ይሸለሙ ነበር።»
የተደነቀ፥ የተወደሰዉ የምርጫ-ሒደት፥ የመራጮች ትዕግሥት ሰኞ ሞባሳ ላይ ሕይወት ማጥፋት፥ ደም ማፋሰሱ አልቀረም።ዛሬ ደግሞ ብዙ ብር የፈሰሰበት የድምፅ መቁጠሪያ የኮምፒዉተር ሥርዓት ተበለሻቷል።
አስመራጭ ኮሚሽኑ ለተፈጠረዉ ችግር ይቅርታ ጠይቆ ድምፁ በእጅ እንዲቆጠር አዟል።ይቅርታ ቆጠራዉ ግን፥ የፖለቲካ ተንታኝ ሙዋሊሙ ማቲ እንደሚሉት የተፎካካሪዎችን ጥርጣሬ፥ የመራጩን ሥጋት የሚያስወግድ አልሆነም።
«የአስመራጭ ኮሚሽኑ ባለሥልጣናት ያጋጠመዉን ችግር በተገቢዉ መንገድ ያስረዱ አይመስለኝም። በዚሕም ምክንያት ሰዎች የሚመስላቸዉን እንዲተነብዩ ቀዳዳ ከፍተዋል።መላምትና ትንበያዉ ደግሞ ከመቁጠሪያዉ መበላሸት ጀርባ ያለፈዉ አይነት ችግር ለመፍጠር ታስቦ ነዉ የሚል አሉታዊ እምነት በሰወች ዘንድ ያሳድራል።»
ነገሩ «ቀን እባብ ያየ ማታ በልጥ በረየ» አይነት ነዉ።ከአምስት ዓመት በፊት የተደረገዉ የምርጫ ዉጤት ዉዝግብ ሰበብ ሺዎች ያለቁ፥ ብዙ ሺዎችን የቆሰሉ፥ መቶ ሺሕዎች የተፈናቀሉበት ኬንያዊ ሙዋሊሙ እንደሚሉት በምንም ነገር ይሰጋል፥ ምንንም ነገር ይጠራጠራል።ጥርጣሬዉ በተለይ በምርጫዉ ብዙ ያልቀናቸዉን ራይላ ኦዲንጋን ለፍርድ ቤት ሙግት ሊያደርስ ይችላል።
«እንደሚገበኝ ከትላልቆቹ ተጣማሪዎች የራይላ ኦዲንጋዉ ጥምረት ድምፁ ከኮሚተር ይልቅ በእጅ መቆጠሩን በፍርድ ቤት ለማስቆም ክስ ሳይመሰርቱ አይቀሩም።»
በዚሕ መሐል ኡሑሩ ኬንያታ የሚመሩት ጥምረት የቀድሞዋ የኬንያ ቅኝ ገዢ ብሪታንያ በምርጫዉ ሒደት ጣልቃ ገብታለች በማለት ወንጅሏል።ፓርቲዉ በኬንያ የብሪታንያ አምባሳደር ክርስቲያን ተርነር ምርጫ ኮሚሽኑ የተበላሹ ብሎ የጣላቸዉ የድምፅ ካርዶች እንዲቆጠሩ መጠየቃቸዉን እንደቀጥታ ጣልቃ ገብነት ነዉ-ያየዉ።
ነጋሽ መሐመድ
ሸዋዬ ለገሠ