የኦሮሚያ ባለስልጣናት የአዉሮጳ ጉብኝት
ረቡዕ፣ ጥር 27 2007ማስታወቂያ
ባለፈዉ ዓርብ ፍራንክፈርት የገቡት ልዑካን በፍርናክፈርትና አካባቢዉ እንዲሁም በበርሊን ከሚገኙ በኢትዮጵያ ኤምባሲ በኩል ጥሪ በተደረገላቸዉና ጥሪዉንም ለመቀበል ፈቃደኛ ከሆኑት ጋ ስበሰባ አካሂደዋል። በስብሰባዉም በኦሮሚያ ስለሚካሄዱ የልማት እንቅስቃሴዎች ገለፃ አድርገዉ ከተሰብሳቢዎቹም ስለዴሞክራሲና የሰብዓዊ መብቶች ይዞታ ለቀረቡ ጥያቄዎች ማብራሪያ መሰጠቱን ባለስልጣኑ አመልክተዋል። የልዑካኑ መሪ በኦሮሚያ ክልል በምክትል ፕሬዝደንት ደረጃ የኦሮሞ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት ኦህዴድ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ዳባ ደበሌ እንደሚሉት በዉጭዉ ዓለም የሚገኘዉን የኦሮሞ ማኅብረሰብ ማነጋገሩ እንግዳ አይደለም። ሆኖም በአሁኑ ወቅት በአዉሮጳና በሰሜን አሜሪካ እንዲሁም በአፍሪቃና በሌሎችም አካባቢዎች የሚገኙትን የኦሮሞ ተወላጆች ለማዳረስ ሰፊ እቅድ ተይዟል። ከጀርመን ቀጥሎም በስቶክሆልም እና ኦስሎ ተመሳሳይ ዉይይት ለማካሄድ በዝግጅት ላይ መሆናቸዉንም አቶ ዳባ ጨምረዉ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ከፍተኛ የዴሞክራሲ ግንባታ ላይ ናት ያሉት የኦህዴድ ባለስልጣን በእሳቸዉ የሚመራዉ ልዑክ ጀርመንን ጨምሮ በተጠቀሱት ሃገራት ለ12 ቀናት እንደሚቆይም አመልክተዋል።
ሸዋዬ ለገሠ
አርያም ተክሌ