1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኤ ሲ ፒ ሀገሮች ጉባዔ በሞዛምቢክ

ዓርብ፣ ሰኔ 11 1996

ከፊታችን ሰኔ አሥራ ሦስት እስከ ሰኔ አሥራ ስድስት ድረስ ሰባ ዘጠኝ የአፍሪቃ፡ የከራይብና የፓሲፊክ አካባቢ ሀገሮች በሞዛምቢክ መዲና ማፑቶ ዓቢይ ጉባዔ ያካሂዳሉ። « ባንድነት የወደፊት ዕጣችንን እንገነባለን« በሚል መፈክር ሥር የሚካሄደውን የማፑቶ ዓቢይ ጉባዔ ወጪ የሚሸፍኑት የሞዛምቢክ መንግሥትና ዓለም አቀፉ ኅብረተ ሰብ ናቸው።

https://p.dw.com/p/E0kw
የኤ ሲ ፒ ሀገሮች ጉባዔ የሚካሄድባት የሞዛምቢክ መዲና ማፑቶ
የኤ ሲ ፒ ሀገሮች ጉባዔ የሚካሄድባት የሞዛምቢክ መዲና ማፑቶምስል P. Reategui

ለጉባዔው ዝግጅት ትልቁን መዋጮ፡ ማለትም ሁለት ሚልዮን ዩሮ የከፈለው የአውሮጳ ኅብረት ነው። እነዚሁ ሀገሮች የመጨረሻውን ዓቢይ ጉባዔ ያካሄዱት በ 1992 ዓም በፊጂ ደሴቶች እንደነበር ይታወሳል።

የአውሮጳ ኅብረት የኤ ሲ ፒ ሀገሮች በመባል ከሚታወቁት አዳጊዎቹ የአፍሪቃ፡ የከራይብና የፓሲፊክ አካባቢ ሀገሮች ጋር በሎሜ ውል በደረሰው ስምምነት መሠረት ከ ወዲህ ተባብሮ በመሥራት ላይ ይገኛል። ሰባ ዘጠኙ የኤ ሲ ፒ ሀገሮች በጊያና መዲና ጆርጅታውን በ 1968 ዓም የሎሜን ውል ከተፈራረሙ ወዲህ መሪዎች ከጥቂት ቀናት በኋላ በማፑቶ የሚያደርጉት ጉባዔ አራተኛው መሆኑ ነው። በዚሁ ዓቢይ ጉባዔ ላይ መሪዎቹ ሀገሮቻቸው ከአውሮጳ ኅብረት ጋር ስለላቸው የጋራ አቋም ይነጋገራሉ። በወቅቱ ያለው የአውሮጳ ኅብረትና የኤ ሲ ፒ ሀገሮች ትብብር ሰኔ ዓም የተደረሰውን የኮቶኑን ውል መሠረት ያደረገ ነው። በዚሁ ውል መሠረት፡ ለሀያ ዓመት የሚዘልቀው የሁለቱ ወገኖች ጉድኝት በያምስት ዓመቱ ይታደሳል። ሁለቱ ወገኖች በሚያቀርብ የማሻሻያ ሀሳብ ላይ አሁን የተጀመረው ድርድር የፊታችን የካቲት ይጠናቀቃል። በድርድሩ የኤ ሲ ፒ ሀገሮች አንድ የጋራ የውሳኔና የትብብር አቋም ለመያዝ ጥረት ጀምረዋል፤ የአውሮጳ ኅብረት ደግሞ የንግዱ ግኙነት እንዲፍታታ፡ ማለትም የግምሩክ ገደብ እንዲነሣ ይፈልጋል። ይሁንና፡ ይኸው የኅብረቱ ፍላጎት የኤ ሲ ፒን ሀገሮች ጥቅም እንደማያስከብር የነዚሁ ሀገሮች መሪዎች ያምናሉ። እንደነርሱ አባባል፡ ባንድ በኩል የግምሩክ ገቢ የብዙዎቹ የኤ ሲ ፒ ሀገሮጭ ዋነኛ የገቢ ምንጭ ሲሆን፡ በሌላ በኩል ደግሞ ኅብረቱ ወደነዚሁ ሀገሮች በኤክስፖርት የሚልከው ግዙፍ ድጎማ የሚያገኘው የግብርና ምርት የኤ ሲ ፒን ሀገሮች የግብርና ዘርፍ እንዳይጎዳ ያሠጋል።

በማፑቶው ጉባዔ ላይ ከሚመከርባቸው ጉዳዮች መካከል የአፍሪቃን መረጋጋትና ልማት የሚያሠጉት ፖለቲካዊና ኤኮኖሚያዊ ውዝግቦች ይገኙበታል። በአህጉሩ ሰላም ለማውረድ የሚወሰዱት ርምጃዎች ዋነኛው የጉባዔው መወያያ ነጥቦች መሆናቸውን የሞዛምቢክ ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ሌዎናርዶ ሲማዎ በማስረዳት፡ አፍሪቃ ድህነትን፡ ኤድስን፡ ወባንና የሣኣምባ ነቀርሳን የመሳሰሉ አሳሳቢ ችግሮች እንደተደቀኑበት ገልፀዋል። የካሪቢክና የፓሲፊክ አካባቢ ሀገሮችን የሚመለከቱ ችግሮች፡ በተለይ የንግዱን ግንኙነት የሚመለከቱትም በሚገባ ትኩረት ተሰጥቷቸው እንደሚመከርባቸው አመልክተዋል። ከዚህ ጎን ደግሞ በልማት ወደ ኋላ የቀሩት የኤ ሲ ፒ አባል ሀገሮች፡ ማለትም የማዕከላይና የምዕራብ አፍሪቃ ሀገሮች መሪዎች ማፑቶው ዓቢይ ጉባዔ ውጭ በመገናኘት በ 2000 ዓም ከአውሮጳ ኅብረት ጋር ሊፈራረሙት ስለሚችሉት የኤኮኖሚ ውል በሰፊው ይወያያሉ።