ሰኞ፣ ኅዳር 26 2009
እንደ ዘገባዎቹ ከሆነ ግን፣ አሁንም የማህበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ፣ ማለትም የዋትስአፕ፣ የቫይበር፣ የፌስቦክና ኢንስታግራም አገልግሎት እንደተዘጉ ይገኛሉ። መንግስት ለዚሁ ርምጃው በኦሮምያና በአማራ ክልል ተከስቶ የነበረዉን ተቃዉሞ ለማርገብ መሆኑን እንደ ምክንያት መጥቀሱ ይታወሳል።
በተለያዩ የኦሮምያና የአማራ ክልል ነዋሪዎች በአካባቢዎች አሁን ያለዉ የኢንቴርኔት አገልግሎት ምን እንደሚመስል ጠይቀናቸዋል። ብዙዎቹ ስማቸው እና ያሉበት ቦታ እንዲጠቀስ ባይፈልጉም አስተያየት ለመስጠት ዝግጁ ነበሩ። አንዱ የአማራ ክልል ነዋሪ፣ ባለፈው ዓርብ ኢንቴርኔት መከፈቱን ቢያረጋግጡም፣ እሳቸው Psiphon በተሰኘዉ የፀረ/ሳንሱር አፕሊልኬሼን እንደሚጠቀሙ ተናግረዋል።
ሌላው የምዕራብ ሃራርጌ የቆቦ ነዋሪ መምህር የኢንቴርኔት ላለፉት ሁለት ወራት መዘጋት በሙያቸዉ ላይ ተፅዕኖ እንደፈጠረባቸው ገልጸዋል። ኢንቴርኔት መልሶ ተከፈተ ቢባልም፣ አገልግሎቱ በትክክክል ይሰራል ማለት አይደለም ይላሉ። «እኔ በፌስቡክ ነዉ የምጠቀመዉ። ባለፉት ጊዚያት ሙሉ በሙሉ አልነበረም። ትላንት ነበረ። እኔ ያለሁበት ቦታ ግን አሁን አይሰራም።»
የአባት ስማቸዉን ለመጥቀስ ያልፈለጉ አቶ አብዲ የተባሉ የአዲስ አበባ ነዋሪ ደግሞ የኢንቴርኔት አገልግሎት በከፊል ተከፈተ ቢባልም ፣ «አዝጋሚ» መሆኑን ነው ያስታወቁት።
የአዳማው ነዋሪ ደግሞ የኢንቴርኔት አገልግሎትን ላለፉት ወራቶች በPsiphon ሲጠቀሙ እንደነበሩ ተናግረው በወቅቱ ከድሮው የተለወጠ ነገር እንዳላዩ አስረድተዋል። መልሶ ተከፈተ የተባለበት አካባቢ በግልፅ አይታወቅም ይላሉ።
በዚሁ ጉዳይ ላይ ከኢትዮጵያ የመንግስት ኮሙኒኬሼን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት መረጃ ለማግኘት ብንሞክርም አልተሳካልንም። መቀመጫዉን በዋሽንግቶን ዲ ሲ ያደረገዉ የአሜሪካውያኑ የብሩክሊን ተቋም ከጥቂት ጊዜ በፊት ያወጣው ጥናት እንዳሳየው፣ የኢትዮጵያ መንግሥት ኢንቴርኔት በመዝጋቱ ወደ ዘጠኝ ሚሊዮን ዶላር አጥቶዋል።
መርጋ ዮናስ
አረያም ተክሌ