የኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ቀዉስ
ማክሰኞ፣ መስከረም 17 2009ኢትዮጵያ ዉስጥ ካለፈዉ ኅዳር ጀምሮ የተቀጣጠለዉን ሕዝባዊ ተቃዉሞ ለመደፍለቅ መንግሥት የሚወስደዉን የኃይል እርምጃ አቁሞ ሰላማዊ መፍትሔ እንዲፈልግ የኢትዮጵያ የመግባባት አንድነትና የሰላም ማሕበር ጠየቀ። የማኅበሩ ዋና ሥራ አስኪያጅ ዛሬ እንዳስታወቁት ማኅበራቸዉ ችግሩ ከመፈጠሩ በፊት ጀምሮ መንግሥት መፍትሔ እንዲፈልግ በተደጋጋሚ ቢጠይቅም እስካሁን የተሰጠ ቀና ምላሽ የለም። የሃይማኖት ተቋማት መሪዎችም ደመፋሰሱን ለማቆም ጣልቃ እንዲገቡ የቀረበላቸዉን ጥያቄ በቀና መንፈስ አልተቀበሉትም። ይሁንና ማኅበሩ ሰላም ለማስፈን የሚያደርገዉን ጥረት አሁንም ይቀጥላል።
የኢትዮጵያ የመግባባት የአንድነትና የሰላም ማኅበር ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ፋንታሁን ብርሃኑ ተቃዉሞ፤ ግጭት፤ ግድያ፤ እስራትና የሐብት ንብረት ዉድመቱን «ችግር» ይሉታል በአንድ ጥቅል ቃል። ችግሩ እንደሚከሰት ማኅበራቸዉ ወትሮም ይሰጋ ነበር።
የማኅበሩን ፤ የሌሎች ወገኖችን፤ የመገናኛ ብዙሃንን ማስጠንቀቂያ መንግሥት «ጆሮ ዳባ ልበስ» በማለቱ፤ ከሁሉም በላይ የሕዝቡን ብሶት ከቁብ ባለመቁጠሩ የተጠራቀመዉ ቅሬታ ወደ ሥርዓት ለዉጥ ጥያቄ ንሯል።-እንደ አቶ ፋንታሁን።
ማኅበሩ፤ አቶ ፋንታሁን እንደሚሉት ከጠቅላይ ሚንስትሩ ቢሮ እስከ ፕሬዝደንቱ ፅሕፈት ቤት፤ ከተወካዮች ምክር ቤት እስከ ፀጥታ መሥሪያ ቤቶች ያሉ የመንግሥት ተቋማትን በደብዳቤ አሳስቧል። ጠይቋል። በአካል ለማስረዳትም ሞክሯል። መልሱ፤-
አቶ ፋንታሁን እንደሚሉት ማኅበራቸዉ ግጭት ግድያዉ እንዲቆም፤ የሃይማኖት አባቶች፤ የሐገር ሽማግሌዎች፤ ምሁራን እና ታዋቂ ሰዎች ጣልቃ እንዲገቡ ለማግባባት ሞክሯል። እየሞከረም ነዉ። ከሃይማኖት ተቋማት መሪዎች የተሰጠዉ መልስ ግን «ተስፋ አስቆራጭ» ነዉ።
የኢትዮጵያ መንግሥት አሁንም ለፖለቲካዊ ቀዉሱ ሰላማዊ መፍትሔ እንዲፈልግ አቶ ፋንታሁን አሳስበዋል።
ነጋሽ መሐመድ
ሸዋዬ ለገሰ