የኢትዮጵያ የኃይል ምንጭ ስብጥር
ማክሰኞ፣ ሚያዝያ 14 2006ኢትዮጵያ ዉስጥ የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦትን አስተማማኝ ለማድረግ የሚከናወኑ ተግባራት ፈርጀ ብዙ መሆናቸዉ ይነገራል። በተለይም የኃይል ስብጥሩን በማብዛት ታዳሽና አረንጓዴ የኃይል ምንጮችን በመጠቀሙ ረገድ ከፍተኛ ጥረቶች እየተደረጉ እንደሆነ እዚህ ጀርመን ሃምበርክ ከተማ በተካሄደዉ የጀርመን አፍሪቃ የኃይል አቅርቦትና ፍላጎት ላይ የሚያተኩረዉ መድረክ ተሳታፊ የነበሩ የዘርፉ ባለሙያ ለዶቼ ቬለ ገልጸዋል።
አስተማማኝ የኃይል አቅርቦት የወቅቱ የዓለማችን ዋነኛ ጥያቄ ሆኗል። እያንዳንዱ ሀገርም ለኤኮኖሚ እድገቱ የሚበጀዉን ዘላቂ የኃይል አቅርቦት ሲያስስ ይስተዋላል። ኢትዮጵያ ከራሷ አልፋ ለጎረቤቶቿ የምትሸጠዉን የኃይል አቅርቦት ለማብዛት የተለያዩ የኃይል ምንጮች ላይ እየሠራች እንደምትገኝ የኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ኃይል የስልትና ኢንቬስትመንት ዘርፍ ኃላፊ አቶ መኩሪያ ለማ ለዶቼ ቬለ ገልጸዋል። መረጃዎች እንደሚሉትም አፍሪቃ በጎርጎሪዮሳዊዉ 2040ዓ,ም የኃይል አቅርቦት መሠረተ ልማቶችን ለመገንባት 1 ትሪሊየን ዩሮ ለዘርፉ ለማዋል ይሻሉ። ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት በከፍተኛ ትኩረት በመገንባት ላይ የምትገኘዉ የሕዳሴ ግድብ ከአንድ ዓመት በኋላ በከፊል ኃልም ማመንጨት እንደሚጀምር ተነግሯል። ከሀገር አልፎ ለጎረቤት ገበያ የሚተርፍ የኤሌክትሪክ ኃይል እንዲያመነጭ የሚጠበቀዉ አባይ ላይ የሚገነባዉ ግድብ ግን የአባይ ዉሃ ድርና ማጓ ለሆነዉ ግብፅ ከፍተኛ ስጋት መፍጠሩ ተደጋግሞ የሚነሳ ጉዳይ ነዉ። በዚህ ምክንያትም ግብፅ በተግባሩ ቅር መሰኘት ብቻ ሳይሆን የኃይል ርምጃም ልትወስድ ትችል ይሆናልም የሚሉ ዘገባዎች ይወጣሉ። የዶቼ ቬለ የአማርኛዉ ቋንቋ ኃላፊ ሉድገር ሻዶምስኪ በኢትዮጵያ ለኃይል አቅርቦቱ አባይ ወንዝ ላይ የሚሠራዉ ግድብ የሚኖረዉን ሚና ጨምሮ፤ ስለኃይል ምንጮች ስብጥር እንዲሁም ታዳሽ የኃይል ምንጮች ምን ያህል ጥቅም ላይ እየዋሉ ነዉ በሚል ላነሳላቸዉ ጥያቄዎች አቶ መኩሪያ የሰጡትን ማብራሪያ፤ ከድምፅ ዘገባዉ ማድመጥ ይቻላል።
ሸዋዬ ለገሠ
አርያም ተክሌ