1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢትዮጵያ ምስቅልቅልና መፍትሔዉ

እሑድ፣ ሰኔ 14 2012

በምርጫ መራዘም-አለመራዘም፣ በሕግ መከበር-መጣስ፣ በክልልነት ጥያቄ መልስ-ማጣት ሰበብ ፖለቲከ ኞችዋ እየተወዛገቡ ነዉ።የጠብ፣ዉዝግብ፣ ግጭቱ ዑደት መሰረታዊ ምክንያት ምንድነዉ? መፍትሔስ አለዉ ይሆን?

https://p.dw.com/p/3e449
Karte Äthiopien Ethnien EN

ውይይት፦ ኢትዮጵያ ከፖለቲከኞችዋ እንካ ሰላንቲያ ትላቀቅ ይሆን?

 

ለባዕድ ሚልኪ አምላኪዎች ዘንድሮ ሰኔ-ከሰኞ ገጥሟል።ሰኔ ከመባቱ ከጥቂት ሳምንታት በፊት የትግራይ ምክር ቤት በክልሉ ምርጫ ለማድረግ ወስኗል።ዉሳኔዉ የክልሉ ገዢ ፓርቲ ሕወሓት እንደ ፓርቲ ከወሰነ-በኋላ የተደረገ በመሆኑ ብዙ የገረመዉ የለም።ካስገረመ ግጥምጥሞሹ ነዉ።አንድ ሁለቱን እንጥቀስ። ጠቅላይ ሚንስትር ዓብይ አሕመድ መንግሥታቸዉ የኮሮና ተሕዋሲን ለመከላከል የደነገገዉ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የሐገሪቱን ሕገ-መንግሥት ማገዱን ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ባስረዱ ሳልስት፣ የፌደሬሽን ምርክ ቤት አፈ ጉባኤ ሥልጣናቸዉን ለቀቁ።ምክንያታቸዉ ያዉ ፓርቲቸዉ ከመቀሌ በተደጋጋሚ ያለዉ ነዉ።«ሕገ-መንግሥት እየተጣሰ፣ አምባገነናዊ መንግስት እየተመሠረተ ነዉ» የሚል።

አፈ ጉባኤዋ ስልጣን ከለቀቁ በኋላ የፌደሬሽን ምክር ቤት፣ ጠቅላይ ሚንስትሩ «ባስቸኳይ አዋጅ ታግዷል» ላሉት ሕገ-መንግሥት ትርጉም ሰጥቷል።ትርጉሙ በስልጣን ላይ ያለዉን መንግሥት፣ዘመነ ስልጣን፣ የምርጫ ጊዜንም ማራዘሙ ነዉ።ዉሳኔዉን በርካታ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ዉድአድርገዉታል።

የሚልየፌደሬሽን ምክር ዉሳኔና ተቃዉመዉ  በተሰማበት ሳምንት በደቡብ ክልል የዎላይታ የምክር ቤት እንደራሴዎች ስልጣናቸዉን በጅምላ ለቀዋል።ምክንያት፣ ጠቅላይ ሚንስትሩ ታግዷል ባሉት ሕገ-መንግስት መሠረት ወላይታ ዞን ያቀረበዉ ክልል የመሆን አቤቱታ መልስ አላገኘም የሚል ነዉ።

የወላይታ እንደራሴዎች ሥልጣን በለቀቁ በአራተኛዉ ቀን የደቡብ ክልል ምክር ቤት የሲዳማ ዞንን የ10ኛ የክልልነትን የስልጣን ርክክብ አፅድቋል።የኃያማኖትና የሐገር ሽማግሌዎች በጣም ያሳሰባቸዉ የመንግስትና የተቃዋሚዎች ዉዝግብ፣ የደቡብ ፖለቲከኞች የክልልነት ጥያቄ፣ የሕገ-መንግስት  አልተተረጎመም-ዉዝግብ ሳይሆን የፌደራሉና የትግራይ መሪዎች እንኪያ ሰላንቲያ ነዉ።የኮሮና ተሕዋሲ ወረርሺም ለአዋዛጋቢዎቹ እርምጃዎች የትክክለኛነት ማረጋገጪያ (ጀስቲፊኬሽን) ከመሆን ባለፍ የሚያጠፋዉን ሕይወት፣ ሚያስከትለዉን ኪሳራ ለሚገታ ትብብር ምክንያት ሲሆን አንሰማም።ኢትዮጵያን ባንዴ ከብዙ ምስቅልቅል የዶለዉ ምንድነዉ? መዉጪያ መንገዱስ? የዛሬ ዉይይታችን ጥያቄዎች ናቸዉ።

ነጋሽ መሐመድ

እሸቴ በቀለ