የአፍሪቃ የፋሽን ሳምንት በአፍሪቃ ህብረት
ዓርብ፣ ሚያዝያ 19 2004የከባቢ አየር ለውጥ በዚሁ ከቀጠለ ወደፊት ምን እንደምንለብስ አስበንበት ይሆን? በዚህ ሳምንት በአዲስ አበባ የአፍሪቃውያን የፋሽን ሳምንት ዝግጅት፤ ትኩረት የሰጠበት አንዱ ርዕስ ነው። ምንም እንኳን የኢትዮጵያ አየር እንደ አውሮፓው ተለዋዋጭ ባይሆንም ከአየሩ ጋ ተስማሚ የሆነ ልብስ መልበስ መቼም ሁላችንም የምንመርጥ ይመስለኛል። በአውሮፓ የሚያዚያ ወር አየር ክፉኛ ተለዋዋጭ ነው። ከዜሮ ዲግሪ ሴንቲ ግሬድ እስከ 30 ዲግሪ -ቁጥሮች የሚፈራረቁበት! ታድያ ከቁም ሳጥናችን ውስጥ የተለያዩ አልባሳትን አውጥተን ለመልበስ እንድንችል የልብስ ቅድ ባለሙያዎች ወይም ዲዛይነርስ እና የልብስ ኢንዱስትሪዎች ወሳኝ ናቸው!
ካለፈው ማክሰኞ ጀምሮ እስከ ዛሬ አርብ ድረስ የአፍሪቃውያን የፋሽን ሳምንት በአዲስ አበባ ተካሂዷል። ዝግጅቱ ከጠበቅነው በላይ እና እጅግ ደስ የሚያሰኝ ነበር ይላሉ ከዝግጁቱ አስተባባሪ አንዷ፤ ሊንዳ ሙሪቲ ። HUB OF AFRICA FASHION WEEK የሚል መጠሪያ ያለው ዝግጅት ሲካሄድ ሁለተኛ ጊዜው ነው። የአሁኑን ትርዒቱ ከበፊቱ ምን ይለየዋል?
« ልዩነቱ በመጀመሪያ ነገር የተሻለ ድጋፍ የሚሰጡ እና የልብስ ቅድ ባለሙያዎች ነበሩን። ያሁኑን ትርዒት ትልቅ የሚያደርገው ሌላው ነገር በአዲሱ የአፍሪቃ ህብረት ህንፃ ውስጥ በመካሄዱ ነው ። የዝግጅቱ ተካፋዮች፣ በቀመጫቸው አፍሪቃ የሆኑት ተወዳዳሪዎች እና ተባባሪዎቻችን በሙሉ ለፋሽን ኢንዱስትሪው ጠንካራ መልዕክት ያስተላልፋሉ ብዬ አምናለሁ።»
የዝግጅቱ አላማ የአፍሪቃን ችሎታ ያላቸው የልብስ ቅድ ባለሙያዎች ማስተዋወቅ ብቻ ሳይሆን፤ ባለሙያዎቹ ከከባቢ አየር ለውጥ ጋ በተያያዘ፣ ስራዎችን እንዲያስተዋውቁ ታዘው ነበር። ባለሙያዎቹ ለፋሽን ኢንዱስትሪው እንዲያስተላልፉ የተፈለገውን ጠንካራ መልዕክት ኬኒያዊቷ ሊንዳ ሙሪቲ ያብራራሉ፤
« የልብስ ቅድ ባለሙያዎች ስለ አፍሪቃ ግንዛቤ እንዲያዳብሩ ለማድረግ ነው ቡድኑ የሚጥረው። ሁሉም ቢያንስ አንድ በቀላሉ በተገኙ መገልገያዎች ተጠቅመው ስራቸውን ለማስተዋወቅ ችለዋል። ይህም የሚያሳየው በአካባቢያችን በቀላሉ ያገኘናቸውን መገልገያዎች ተጠቅመን የዚያኑ ያህል መገልገያዎች መስራት እንደሚቻል ነው። እንዲሁም የልብስ ቅድ ባለሙያዎቹ በአፍሪቃ የፋሽን ሳምንት እንዲሳተፉ ለማድረግ ችለናል።»
አፍሪቃውያን የልብስ ቅድ ባለሙያዎች ለታዋቂ የፋሽን ድርጅቶች አርዓያ በመሆን ፤ አየር ንብረትን በማይበክሉ መገልገያዎች ምን መስራት እንደሚቻል እንዲያስተዋውቁ እንፈልጋለን ይላሉ ሊንዳ ሙሪቲ። በዝግጅቱ ላይ ከተለያዩ የአፍሪቃ ክፍል የመጡ ባለሙያዎች እና ሞዴሎች ተሳትፈዋል። የአፍሪቃውያን የፋሽን ሳምንት ዘንድሮም በአዲስ አበባ ነው የተዘጋጀው። አዘጋጆቹ ለምን አዲስ አበባን መረጡ?
« አዲስ አበባ እንዲዘጋጅ የተፈለገበት ምክንያት በመጀመሪያ አዲስ አበባ ዋና ከተማ ናት። ከዚህም ሌላ ከአፍሪቃ በርካታ ኤምባሲዎች የሚገኙባት ከተማ በመሆኗ ነው። ከአለም አቀፍ እንደ ለንደን እና ዋሽንግተን ዲሲ ከተማዎች ቀጥሎ ማለት እችላለሁ። እንዲሁም የአፍሪቃ ህብረት መቀመጫ ናት፣ ማንኛውም አይነት ውሳኔ በአዲስ አበባ ነው የሚወሰነው። ለዚያ ስንል ነው ለውጦች በሚካሄዱበት ከተማ ለማድረግ የወሰነው።»
በዚሁ አራት ቀናት በቆየው የፋሽን ትርዒት ላይ ከጋና፣ ታንዛኒያ፣ኬኒያ የመሳሰሉ የአፍሪቃ ሀገሮች የልብስ ቅድ ባለሙያዎች ተካፍለዋል። ከእንግዳ ተቀባይዋ ሀገር ኢትዮጵያ ፤ ማህሌት አፎወርቅን እና ኦስማን መሐመድን ለዛሬ አነጋግረናል። ስለአስተዋወቁት ስራ አጫውተውናል። ከዘገባው ያገኙታል።
ልደት አበበ