የአፍሪቃ እና የአውሮጳ ኅብረት ጉባዔ እና ወጣቱ
ረቡዕ፣ ኅዳር 20 2010ከ80 የሚበልጡ አፍሪቃውያን እና አውሮጳውያን ርዕሳነ ብሔር እና መራህያነ መንግሥት፣ እንዲሁም፣ የአውሮጳ ኅብረት ኮሚሽን ፕሬዚደንት የሚገኙበት ይኸው የአቢዦን ጉባዔ ለዘላቂ እድል በወጣቱ ላይ አትኩሮ መስራት የሚል መሪ ቃል ይዟል። በዚሁ ጉባዔ ላይ አፍሪቃን እና አውሮጳን የወከሉ ወጣቶች ባለፈው ጥቅምት ወር በኮት ዲቯር አቢዦን ያዘጋጁትን ሰነድ ለመሪዎቹ ያቀርባሉ። 36 ወጣቶች የተጠቃለሉበት ቡድን ለመሪዎቹ በሚያቀርቡት ሰነድ ውስጥ፣ በተለይ ለነርሱ እና አህጉሩ አቻዎቻቸው ትልቅ ትርጓሜ ይዘዋል ባሏቸው በትምህርቱ እና በሙያ ስልጠናው፣ በኤኮኖሚ እና በስራ ፈጠራ፣ እንዲሁም፣ ፍልሰት እና የፀጥታ ጥበቃን በመሳሰሉ ጉዳዮች ሊደረጉ ይገባሉ ያሏቸው ሀሳቦች በዝርዝር ቀርበዋል። በአቢዦን ከተገኙት ወጣቶች መካከል ኢትዮጵያዊቷ ፌበን ታምራት ጉባዔው በስራ ፈጠራው ላይ ወጣቱን የሚጠቅም ውጤት እንዲያስገኝ እንደምትጠብቅ ገልጻለች።
« በአፍሪቃ ኅብረት እና በአውሮጳ ኅብረት መካከል አጋርነቱ የሚታደስበት ሁኔታ የተሻለ ኑሮ ለማምጣት፣ ወጣቶች ያነቋቁዋቸው እቅዶችን ለማገዙ እና ለወጣቶቹ ዘላቂ የስራ እድል በመፍጠር ወጣቶችን በየሀገራቸው ለማቆየት ይርዳል ብዬ አስባለሁ። »
ከስዋዚላንድ የሄደችው ኖንዲሚ ሲሾብፌም በጉባዔው የተሳተፉት መሪዎቹ ወጣቶቹ ላቀረቧቸው ሀሳቦች አዎንታዊ ምላሽ እንደሚሰጡ ተስፋቸውን አድርጋለች።
« ያቀረብናቸውን ሀሳቦች ይቀበላሉ ብለን ተስፋ አድርገናል። ድምፅ የሌላቸውን የአህጉራችን ወጣቶች ድምፅ ይዘን ነው የመጣነው። ስለዚህ መደመጥ እንፈልጋለን። ይህን ጥያቄያችንን እንደሚሰሙ እና ሀሳባችንን ገቢራዊ እንድናደርግ እድሉን እንደሚሰጡን ተስፋ አለኝ። »
የአውሮጳ ኅብረት የውጭ ጉዳይ ተጠሪ እና የኮሚሽኑ ምክትል ፕሬዚደንት ፌዴሪካ ሞጌሪኒ መሪዎቹ ወጣቶቹን የማዳመጥ ኃላፊነት እንዳለባቸው ገልጸው፣ ጥሩ የወደፊት እድል በመፍጠሩ ረገድ ወጣቱን ተሳታፊ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን አስታውቀዋል።
ከአህጉራት ሁሉ ወጣት በምትባለው አፍሪቃ ውስጥ ከሚኖረው ሕዝብ መካከል ወደ 60% የሚጠጋው ከ25 ዓመት በታች የሆኑ ወጣቶች ናቸው።
አርያም ተክሌ
ሸዋዬ ለገሠ