የአፍሪቃ መሪዎች ጉባዔና ኮንጎ፣
ሐሙስ፣ ነሐሴ 3 2004
በምሥራቅ ኮንጎ የተቀሰቀሰውን የትጥቅ አመጽ፤ በገልልተኛ አመጽ ለማረቅ ካምፓላ ላይ የመከሩት የአፍሪቃ መሪዎች፤ ለጊዜው መፍትኄ ሳያስገኙለት እንደገና በአንድ ወር ለመሰብሰብ ተስማምተው ነው ትናንት የተለያዩት። M 23 በመባል በታወቀው አማጺ ኃይልና በኮንጎ መንግሥት ወታደሮች በኩል በተደረገ ውጊያ ሳቢያ፣ ከሞላ ጎደል ግማሽ ሚሊዮን ህዝብ ነው ከቀየው የተፈናቀለው። ስለምሥራቅ ኮንጎና ፤ ለጊዜው አልባት ስልልተደረገለት ውዝግብ ፤ ተክሌ የኋላ የሚከተለውን አጠር ያለ ዘገባ አጠናቅሯል።
የታላላቆቹ ሀይቆች አካባቢ መንግሥታት መሪዎች፤ በኮንጎ የተሠማሩትን አማጽያን እንቅሥቃሴ ለማረቅ፤ ቀደም ሲል በተስማሙት መሠረት ካምፓላ ፤ ዩጋንዳ ላይ ፣ ከማክሰኞ አንስተው እስከትናንት ለ 2 ቀናት ቢመክሩም፤ ስምምነት ላይ ሳይደርሱ ነበረ የተለያዩት። እንደሚባለው ከሆነ ውዝግቡ ውስብስብ ያለ በመሆኑ ፤ በላጋሽ አገሮች ግፊት ብቻ የሠመረ ውጤት ማግኘት መቻሉ ከመጀመሪያውም የተጠራጠሩ ነበሩ።
የኮንጎ የማስታወቂያ ሚንስትር ላምቤ ሜንደ ግን ፤ ተስፋ በማድረግ እንዲህ ነበረ ያሉት፤
«የሚያሳዝነው ፤ ጎረቤቶቻችን የሩዋንዳ ነጻ አውጭ ኃይል (FDLR)የተሰኘውን እንጂ M 23 የተባለውን መውጋት አይገባም የሚል አቋም ነበረ የሚያራምዱት፤ ህዝቡ ግን በ FDLR ም በ M 23 ም ነው የሚገደለው። ስለሆነም ሁለቱንም ንቅናቄዎች ማጥፋት አለብን። ያም ሆነ ይህ አዲስ አበባ ላይ ጉዳዩ ተንቀሳቅሶ፤ ፕሬዚዳንት ካጋሜም m 23 ጭምር አሉታዊ ኤይል መሆኑን በደነገገው ሰነድ ላይ ፈርመዋል። እንድ በጎ እርምጃ አለ ማለት ነው።»
ግራም ነፈሰ ቀን፤ በካምፓላ ዓለም አቀፍ ጉባዔ የተገኙት የ 11 አባል ሃገራት ተጠሪዎች፤ ለውዝግቡ «አገር በቀል መላ » ለመፈለግ ተስማምተው ነው የተለያዩት። ከተጠቀሱት አገሮች መካከል የ 7,ቱ ሃገራት የመከላከያ ሚንስትሮች፣ የሩዋንዳና የኮንጎ ዴሞክራቲክ ሪፓብሊክ ጭምር ፣ ምን ያህል ሰላም አስከባሪ ወታደሮች እንደሚያስፈልጉ የስንቅና ትጥቁንም መጠን አስልተው ከ 4 ሳምንት በኋላ ለመሪዎቹ ጉባዔ የሚያቀርቡ መሆናቸውን የዩጋንዳው ፕሬዚዳንት ዮዌሪ ሙሴቬኒ አስታውቀዋል። የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታ ጥበቃው ም/ቤት ፣ በቱስሲዎች ለሚመራው M 23 ለተሰኘው አማጺ ኅይል ድጋፍ መስጠት ይቁም ሲል ጥያቄ ያቀረበ ሲሆን ፣ ተግሳፁ ሩዋንዳንና ዩጋንዳን የሚመለከት እንደነበረ ተመልክቷል። ሩዋንዳም ፤ ዩጋንዳም ለ M 23 መሣሪያም ሆነ የሚመለመሉ ወታደሮች አለማቅረባቸውን የገለጡት። ውዝግቡን ፣ ከታላላቆቹ ሀይቆች አዋሳኝ ሀገራት የተውጣጡ ወታደሮች ፤ የM 23 ን እንቅሥቃሴ እንዲገቱ ፕሬዚዳንት ጆሰፍ ካቢላ ቢስማሙም የመከላከያ ሚንስትሩ አሌክሳንደር ሉባ እንታምቦ ይህ እውነት ነው ሲሉ አለማረጋገጣቸውን ፤ የዩጋንዳው ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ሄንሪ ኦኬሎ ኦሪየም ተናግረዋል።
በኮንጎ 17 ሺ የተባበሩት መንግስታት ሰላም አስከባሪ ጦር እንደተሠማራ የሚገኝ ቢሆንም ወርቅ፤ መዳብ፣ ቆርቆሮ፣ አላማዝና ሌሎችም የከበሩ ማዕድናት የሚገኝባትን ግዙፍ ሀገር ፀጥታ ሙሉ በሙሉ ለማስከበር እንደተሳናቸው ነው የሚኙት። ለዚህም ነው ከአካባቢው መንግሥታት የተውጣጣ ኃይል በምሥራቅ ኮንጎ ሰላም እንዲያስከብር የተፈለገው።
የዩናይትድ እስቴትስ ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ሂልሪ ክሊንተን፤ ከትናንት በስቲያ፤ ሩዋንዳና ሌሎች የታላላቆቹ ሀይቆች አካባቢ መንግሥታት፣ M 23 ን ከመደገፍ እንዲቆጠቡ መጠየቃቸው የሚታወስ ነው። ለጋሽ መንግስታት፤ ዩናይትድ እስቴትስና ብሪታንያ፣ ኔደርላንድና ጀርመን ለሩዋንዳ የሚሰጡትን የገንዘብ እርዳታ፤ አማጽያኑን ትደግፋለች በማለት በከፊል መቀነሣቸውን አስታውቀዋል።
ተክሌ የኋላ
ሂሩት መለሰ