የአፋር አካባቢ የስኳር ልማትና ተቃዉሞዉ
ረቡዕ፣ ሚያዝያ 24 2004
በአፋር መስተዳድር ለሱካር ልማትና ለሸንኮራ አገዳ ተክል በሚል ሰበብ በሺሕ የሚቆጠሩ ሰዎች መፈናቀላቸዉንና ካአካባቢዉ አንለቅም ባሉት ነዋሪዎች ላይ የተወሰደዉን እርምጃ አንድ የአካባቢዉ የሠብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት ተቃወመ።መንበሩን ብራልስ-ቤልጂግ ያደረገዉ የአፋር የሠብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት እንደሚለዉ ለሸንኮራ አገዳ ተክል በሚል በሺሕ የሚቆጠሩ አርብቶ አደሮች ተፈናቅለዋል።መፈናቀሉን ከተቃወሙ መካካል ደግሞ ቢያንስ አንድ ሰዉ በፀጥታ ሐይሎች ተኩስ ተገድሏል፥ ሴቶች ጭምር ቆስለዋል።ሌሎች ታስረዋል።ነጋሽ መሐመድ የድርጅቱን ፕሬዝዳት አቶ ጋዓስ አሕመድ ኑርን አነጋግሯቸዋል።
አቶ ጋዓስ አሕመድ ኑር።የአፋር የሠብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት ፕሬዝዳት።አቶ ጋዓስ
እንደሚሉት የሽሜግሌዎቹ አቤቱታ ሁኔታዉን ለመለወጥ የፈየደዉ ነገር የለም።እንዲያዉም ከየቀየዉ እንዲነሳ የሚቀርብለትን ጥያቄ አልቀበልም ያለዉ ወይም ካሳ የጠየቀዉ ወገን የሐይል እርምጃ ይወሰድበት ገባ።
የፀጥታ አስከባሪዎቹ የሐይል እርምጃ ሰዎችን ከቤት-መንደራቸዉ አስገድዶ መዉሰድ ብቻ አልነበረም። እስራት፥ ድብደባ የታከበለበት ጭምር እንጂ።ክፉኛ ከተደበደቡት መሐል ሁለቱ እመጫት ለመሆናቸዉ መረጃ አለን ይላሉ አቶ አጋዓስ።
ፀጥታ አስከባሪዎች በሌላ ቀን ሌላ ስፍራ በወሰዱት የሐይል እርምጃ ደግሞ የሰዉ ሕይወት ጠፍቷል።
ለሽንኮራ አደገዳ ልማት የተከለለዉ ምድር አቶ ጋዓስ እንደሚሉት ለአዋሽ ወንዝ ቅርብ የሆነዉ ሥፍራ ነዉ።ከዚሕ ስፍራ ነዉ አፋር ልቀቅ የተባለዉ።ወይም አትድረስ የተባለዉ።የአፋርን አርብቶ አደርን ከአዋሽ ወንዝ ግራ ቀኝ ርቀሕ ኑር ማለት አቶ ጋዓስ እንደሚሉት እለቅ ከማለት እኩል የሚቆጠር ነዉ።
የአፋር የሠብአዊ መብት ድርጅት ላቀረበዉ ለዚሕ ወቀሳ የአፋር ርዕሠ መስተዳድር አቶ ኡስማኢል ዓሊ ሴሮ መልስ እንዲሰጡን በስልክ ጠይቀን ነበር።በቀጥታ ሥርጭት ከሚደረግ ቃለ-መጠይቅ በስተቀር መልስ እንደማይሰጡን ገልፀዉልናል።የቀጥታ ስርጭት ቃለ-መጠይቁን ለማድረግ ለዛሬዉ ጊዜዉም ቴክኒኩም አልፈቀደልንም።
ነጋሽ መሀመድ
ሒሩት መለሰ