1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአጼ ቴዎድሮስ ሹሩባ መመለስ

ረቡዕ፣ መጋቢት 11 2011

ብሪታንያ ከዛሬ 150 ዓመት በፊት ከንጉሠ-ነገሥት ዳግማዊ አጼ ቴዎድሮስ አስከሬን ላይ የወሰደችውን ፀጉራቸውን ዛሬ ለኢትዮጵያ ታስረክባለች። የርክክብ ሥነ-ስርዓቱም ማምሻውን ርዕሰ ከተማ ለንደን በሚገኘው የብሪታንያ ብሔራዊ  ጦር ቤተ-መዘክር እንደሚካሄድ ብሪታንያ የሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ በድረ-ገጹ ይፋ አድርጓል።

https://p.dw.com/p/3FNs9
Großbritannien National Army Museum in London | Versteigerung des Haares von König Tewodros
ምስል DW/H. Demisse

የባህል ሚኒስትሯ ተረክበዋል

ቅርሱን ለመረከብ ለንደን የሚገኙት የኢትዮጵያ የባህል የቱሪዝም እና የወጣቶች ሚኒስትር ዶክተር ኂሩት ካሳው ከብሪታንያ ቤተ-መዘክር ጋር የመግባቢያ ሰነድ ፈርመዋል። የመግባቢያ ሰነዱ ብሪታንያ እና ኢትዮጵያ በጥናታዊ ጉዳዮች እና በአቅም ግንባታ ዙሪያ በትብብር ለመሥራት ያስችላቸዋል ተብሏል። ለርክክቡ ብሪታንያ የሚገኙት የኢትዮጵያ የባህል የቱሪዝም እና የወጣቶች ሚንሥትር የሕዝብ እና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ገዛኸኝ አባተ የዛሬው ርክክብ ወደፊትም ሌሎች ቅርሶችን ለመረከብ መንገድ ከፋች እንደኾነ ተናግረዋል። «ለወደፊቱ ሌሎች ቅርሶችንም ለማስመለስ በር ይከፍታል።» ብሪታንያ የዛሬ 151 ዓመት አጼ ቴዎድሮስ ያሰሩዋቸውን አውሮጳውያን ለማስለቀቅ ዘመቻ በከፈተችበት ወቅት የኢትዮጵያ ሐብት ተመዝብሯል። ያኔ በሽጉጣቸው ራሳቸውን ያጠፉትን የአጼ ቴዎድሮስ ፀጉር እንዲሁም የተለያዩ በርካታ የኢትዮጵያ ቅርሶችና ሀብቶች ተዘርፈው ወደ ብሪታኒያ ተወስደዋል። ብሪታንያ የተወሰደው የንጉሠ-ነገሥቱ ልጅ ልዑል ዓለማየሁም በ18 ዓመቱ እዚያው ተቀብሯል። የልዑሉን አጽም እና በብሪታንያ የተዘረፉ የኢትዮጵያ ቅርሶችን ለማስመለስ የኢትዮጵያ የባህል እና ቱሪዝም ሚንስቴር እንዲሁም የኢትዮጵያ ኤምባሲን ጨምሮ በርካታ ለሀገር ተቆርቋሪ አትዮጵያውያን ሲሟገቱ ቆይተዋል።

ሃና ደምሴ/ማንተጋፍቶት ስለሺ

አዜብ ታደሰ