«የአይ ኤስ» ቡድንን የመዋጊያ ስልት
ማክሰኞ፣ ጳጉሜን 4 2006ሰሜን እና ደቡብ ኢራቅ እንዲሁም ሰሜን ምስራቅ ሶርያ በተለይ ለሱኒ የ«አይ ኤስ» አክራሪ ቡድን ቅርብ ናቸው። የታጣቂው ቡድን ተፋላሚዎች ከባድ የጦር መሣሪያቸውን በቀላሉ እና እንደፈለጉ ከኢራቅ ወደ ሶሪያ ማሸጋገር ይችላሉ። ስለሆነም የዩናይትድ ስቴትስ የአየር ጥቃት ብቻ ይህንን ቡድን አያዳክምም ይላሉ አንድሬ ባንክ። ባንክ የጀርመኑ የዓለም ዓቀፍና አካባቢያዊ ጥናቶች ተቋም በምህፃሩ GIGA የመካከለኛው ምስራቅ ባልደረባ ናቸው። « ለመካከለኛ እና ዘላቂነት ላለው ጊዜ «የአይ ኤስ» ቡድንን ከአካባቢው ሙሉ ለሙሉ ለማጥፋት ከተፈለገ ሰፊ ስልት ይጠይቃል። በዚህ አክራሪ በሆነው ቡድን ላይ ወታደራዊ ርምጃ ያሻል፤ ይህ ሲሆን ግን ሶርያ ያለውን የመሸሻ ምሽጋቸውን መቆጣጠር ያስፈልጋል። ምክንያቱም ቡድኑ ሶርያ ውስጥ አንድ ሶስተኛውን የሀገሪቱ ክፍል በቁጥጥሩ ስር አድርጎ ይገኛል። በተለይ ሰሜን ምስራቃዊውን ክፍል።»
ይሁንና ልክ እንደ ኢራቅ ሶርያ ውስጥ ቡድኑን ለመዋጋት ፖለቲካዊ መስፈርቱ አልተሟላም። ዩናይትድ ስቴትስ የኢራቅ መንግሥት ትብብርን ተቀብላ ኢራቅ ውስጥ እንደዘመተችው ለሶርያ የማይታሰብ ነው። የፕሬዚዳንት ባሺር አል አሳድ መንግሥት ከምዕራብ ሀገራት ጋር አይዋደድም። ሩሲያ እና ኢራንም ቢሆኑ የምዕራብ ሀገራት እና የአረቡ ሀገራትን ሀሳብ አልተቀበሉትም። ሩሲያ የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት ያቀረበውን የመፍትሄ ሀሳብ በተደጋጋሚ በድምፅ መሻሯ ይታወሳል። ይህ ግን የሶሪያ መንግሥትን በተመለከተ ነበር። አሁን «የአይ ኤስ» ቡድንን በተመለከተ የምዕራቡ ሀገራት ፣ ሩስያ እና ኢራን ተመሳሳይ አመለካከት ነው ያላቸው ይላሉ የሀምቡርግ ከተማው ተመራማሪ። አንድሬ ባንክ« ግን እንደዚያም ሆኖ «የአይ ኤስ» ቡድንን በመዋጋቱ ረገድ በምዕራቡ ሀገራት፣ በሩሲያ እና ኢራን መካከል ፉክክር ይታያል። በተለይ ቅዱስ ጦርነት የሚባለውን እናካሂዳለን የሚሉት ጂሃዲስቶች የያዙት አክራሪ እስልምና በሺዓቶች ላይ ያነጣጠረ ሲሆን በዚህ ረገድ ዩናይትድ ስቴትስንና የጋራ አቋም አላቸው። ሩስያም እንዲሁ አማፂያኑ ጥቃት ሊጥሉ ይችላሉ የሚል ተመሳሳይ ሁኔታ ነው ያለው። »
እንደ አንድሬ ባንክ፤ የሶርያ መንግሥት «የአይ ኤስ» ቡድን እንደ አሁኑ ተጠናክሮ ባይሆንም በሀገሪቱ እንዲቆይ ይፈልጋል ። ምክንያቱም ገዢው የሶርያ መንግሥት ይህንን አማፂ ቡድን እየተዋጋሁ ነው ብሎ ማሳየት ይፈልጋልና ይላሉ ባንክ።በሌላ በኩል የብሪታንያው ሮያል ዩናይትድ ሰርቪስ ተቋም ምክትል ሀላፊ ሚሻኤል ሽተፈንስ ፤ በመቀጠል ዩናይትድ ስቴትስ አማፂ ቡድኑን እንዴት ለመዋጋት እንዳቀደች ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ዕሮብ መግለጫ መስጠት ይጠበቅባቸዋል ይላሉ « ኦባማ ስልታዊ የሆኑ ሶስት ዋና ዋና ጉዳዮችን መዘርዘር ይኖርባቸዋል። አንደኛ ወታደራዊው ተልዕኮ ሞን እንደሚመስል? ፣ ለምን ያህል ጊዜ እንደሚዘልቅ? እና ስለ ስኬት ማውራት የሚቻለው መቼ እንደሆነ? በሁለተኛ ደረጃ ከፕሬዚዳንቱ መስማት የሚጠበቀው ሙስሊም ሱኒዎች የሚኖሩበት ሀገራት እንዴት በዚህ ወታደራዊ ርምጃ ሊካተቱ ታስቧል የሚል ነው? ምን ዓይነት ሚና ይጫወታሉ? ሶስተኛ ሰብዓዊ እቅድ ያሻል? ካሻስ የእነዚህን አከባቢዎች ሰላም መልሶ ለማስፈን ይህ እቅድ ምን ይመስላል? የሚሉ።
ኢራቅ ውስጥ ሱኒዎች የተጠናከሩት ሺዓዎች ጨቁነውናል ሲሉ ነበር። እንደዛም ሆኖ ኢራቅ ውስጥ አንድ የሆነ የሀገር ስሜት ይስተዋላል ይላሉ ሽቴፈን። ይህብ ከሶርያ ጋር ሲያነፃፅሩት ለሽቴፈን ሶርያን እንደ አንድ ሀገር ለመመልከት ይከብዳል።«የአይ ኤስ ቡድን ከተሸነፈ ፤ በመቀጠልስ ምን ይመጣል? በነሱ ቦታ ማን ይተካል? ገዢው መንግስት ሙሉ ቁጥጥሩን ይረከባል ማለት ነው? ሶርያ በተለይ ራካ እና ዴር አል ሶር ከተማ የሚገኙት ነዋሪዎች ይህንን ይቀበላሉ ለማለት ያዳግተኛል።»
አንቶኒያ ቡም / ልደት አበበ
ተክሌ የኋላ