የአቶ ደመቀ መኮንን ፖለቲካዊ ስብእና
ዓርብ፣ የካቲት 23 2010
ጠቅላይ ሚንስትር ኃይለማርያም ደስ አለኝ የስልጣን መልቀቅያ ደብዳቤ ካስገቡ በኋላ የኢትዮጵያ ገዥ ፓርቲ ኢህአዴግ በምትካቸዉ አዲስ ጠቅላይ ሚኒስትር ለመምረጥ በዝግጅት ላይ መሆኑ እየተነገረ ነዉ። የወደፊቱ ጠቅላይ ሚንስትር ይሆናሉ ተብለዉ ከሚገመቱት ፖለቲከኞች አንዱ ያሁኑ ምክትል ጠቅላይ ሚንስትር እና የብአዴን ሊቀመንበር ሆነው ባሉበት እንዲቀጥሉ በቅርቡ ፓርቲያቸዉ የወሰናላቸዉ አቶ ደመቀ መኮንን ናቸዉ። የአቶ ደመቀ ፖለቲካዊ ስብዕናቸዉ ምን ይመስላል?
በወሎ ክፍለ ሐገር የተወለዱት አቶ ደመቀ መኮንን በሕጻንነታቸዉ በደርግ ዘመነ መንግስት በነበረዉ የሰፈራ መረሐ ግብር አገዉ አዊዞን ወደ ምትገኘዉ ቻግኒ ወረዳ መዛወራቸዉን የሕይወት ታሪካቸዉ ያስረዳል። እንደማንኛዉም የገጠር ልጅ በዚሁ አካባቢ የአንደኛና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸዉን አጠናቀዉ፤ በ 1980 ከአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ በባዮሎጂ የትምህርት ዘርፍ የመጀመርያ ዲግሪአቸዉን አግኝተዋል።
የአቶ ደመቀ መኮንን በደጋ ዳሞት ወረዳ ምዕራም ጎጃም ዞን፤ ፈረስ ቤት ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የባዮሎጂ ትምህርት መምህር ሆነዉ አገልግለዋል። በመለጠቅ በቡሪ በቀድሞ አገረ ገዥ በሆኑት በቢትወደድ መንገሻ አትክም በሚጠራዉ ትምህርት ቤት ዉስጥ በመምህርነት ሲያገለግሉ ዛሬ የሦስት ልጆች እናት የሆኑትን ባለቤታቸዉን እና የዚያን ጊዜዋን ተማሪያቸዉን የተዋወቁት።
አቶ ደመቀ የብአዴን/ኢአዴግ አባል ከሆኑ በኋላ በአማራ ክልል በተለያዩ ኮሚሽኖች እና ቢሮዎች በኃላፊነት ሥርተዋል።የአማራ ክልላዊ መንግሥት ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ሆነዉ አገልግለዋል። በዚሁ ስልጣን ላይ ሳሉ በግጭት አፈታት ዘርፍ ሞያ የማስትሪት ድግሪያቸዉን ለማግኘት ወደ ብሪታንያም አቅንተዉ ነበር።አቶ ደመቀ የኢትዮጵያ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል እና የ ትምህርት ሚኒስትር ሆነዉ አገልግለዋል። ከሰኔ ከ2005 ዓ,ም ጀምሮ ደግሞ የኢፌዴሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነዉ በማገልገል ላይ ይገኛሉ። በአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ የሕግ ባለሞያ የሆኑት አቶ ዉብሸት ዉበት፤ ስለአቶ ደመቀ መኮንን አስተያየታቸዉን ሰጥተዉናል።
በመቀሌ ዩንቨርስቲ የህክምና ባለሞያ አለጌታ አብይ የአቶ ደመቀ መኮንን የፖለቲካ ስብእና ለጠቅላይ ሚኒስትርነት በቂ አይመስለኝም ባይ ናቸዉ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን አንድ ወቅት ይህን ተናግረዉ ነበር። « ኤህአዴግን ስቀላቀል ምንም አይነት የፖለቲካ ልምድ አልነበረኝም » ሲሉ ተናግረዉ ነበር። በዩንቨርስቲ የሥነ-ጥበብ ታሪክ መምህር የሆኑት ተባባሪ ፕሮፊሰር አበባዉ አያሌዉ በበኩላቸዉ። በቅርቡ ለአንድ ወር ያህል በባህር ዳር ከተማ የተካሄደውን የብአዴን ማዕከላዊ ኮሚቴ ስብሰባ መጠናቀቅ ተከትሎ የወጣው መግለጫ የብአዴን ማዕከላዊ ኮሚቴ አቶ ደመቀ መኮንን የድርጅቱ ሊቀመንበር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ደግሞ ምክትል ሊቀመንበር ሆነው ባሉበት እንዲቀጥሉ መሰኑ ይታወቃል። ብአዴን አቶ ደመቀ መኮንን የድርጅቱ ሊቀመንበር አድርጎ ባሉበት እንዲቆዩ ያደረገው በተተኪ ጠቅላይ ሚኒስትርነት እጩ አድርጎ ለማቅረብ ስለመሆኑ የገለጸው ነገር የለም።
አዜብ ታደሰ
ነጋሽ መሐመድ