1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

 የአማራ ፀጥታና የባለስልጣናት ቃል

ረቡዕ፣ ሚያዝያ 23 2011

ሁሉም ኢትዮጵያውያን ተከባብረውና መብታቸው ተጠብቆ የሚኖርባት ስርዓት መገንባት እንደሚያስፈልግም በመግለጫቸው አስረድተዋል፡፡ በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስ መምህር አቶ ቻላቸው ታረቀኝ እንደሚሉት ደግሞ እተሰበሰቡ መምከሩ ጥሩ ቢሆንም ወደ ተግባር ካልተቀየረ ግን አሁንም የሚመጣ ለውጥ የለም ይላሉ፡፡

https://p.dw.com/p/3Hlg3
Äthiopien Bahir Dar - stellvertretender Premierminister Demeke Mekonnen
ምስል DW/A. Mekonne

የአማራ ክልል ግጭትና የባለስልጣናት የተስፋ ቃል

የኢትዮጵያ የጦር ኃይል፣ የመረጃና የፀጥታ ከፍተኛ አዛዦችና ባለሥልጣናት በአማራ ክልላዊ መስተዳድር በየጊዜዉ የሚቀሰቀሰዉን ግጭትና ሁከት ለማስቆም ይረዳል ያሉትን ዉይይት ትናንት ባሕር ዳር ዉስጥ አድርገዋል።በዉይይቱ ማብቂያ ምክትል ጠቅላይ ሚንስትር ደመቀ መኮንን ለጋዜጠኞች እንደነገሩት ግጭቶችን ያባብሳሉ የሚባሉ ኃይላትን በተለይም የመንግሥት ባለስልጣናትን የሚያጣራና ለፍርድ የሚያቀርብ ኃይል ተሰማርቷል።አንድ የፖለቲካ ተንታኝ እንዳሉት ግን የመንግስት ባለሥልጣናት ግጭት ግድያዉን ለማስቆም ሁነኛ እርምጃ ካልወሰዱ ዉይይትና መግለጫዉ የሚተክረዉ የለም። የባሕርዳሩ ወኪላችን ዓለምነዉ መኮንን ዝርዝር ዘገባ ልኮልናል።

በአማራ ክልል ለውጡን ተከትሎ በተከሰቱ ግጭቶች የአማራ ክልልን ጨምሮ በተለያዩ ክልሎች ከማንነት ጋር በተያዘ በርካታ የክልሉ ተወላጆች ለስደት፣ ለመፈናቀል፣ ለአካል ጉዳትና ለሞት ተዳርገዋል፡፡

ከዓመቱ መጀመሪያ ጀምሮ በበኒሻንጉል ጉሙዝ፣ በምዕራብና ማዕከላዊ ጎንደር ዞኖች፣ በከሚሴና አጣዬ፣ ሰሞኑን ደግሞ እንደገና ባገረሸው በበኒሻንጉል ጉሙዝ መተከል ዞን በተፈጠሩ ግጭቶች በርካታ ህይወት መጥፋቱንና መፈናቀሉን ምክትል ጠቅላይ ሚኒሰትር አቶ ደመቀ መኮንን አስታውሰዋል፡፡

አቶ ደመቀ እንደሚሉት በዚህ ዘመን በታሪካችን የማናውቀው የጭካኔ ድርጊቶች የተበራከቱበት ጊዜ ነው፡፡ በመሆኑም እየተገነባ ባለው ስርዓት በሰው አስተሳሰብ ምን ተዘራ፣ ወደዚህ አቅጣጫስ ለምን እንሄዳለን የሚለው በዝርዝር እንዲታወቅ ተደርጎ ማረም እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል፡፡

ለተፈጠሩ ችግሮች ተጠያቂው ራሱ መንግስት መሆኑን አቶ ደመቀ ጠቁመው የመንግስትን ቁመና  የሚረጋግጥ ስምሪት ማድረግ እንደሚገባም አመልክተዋል፡፡

በአንድ ጉዳይ ላይ አንደራደርም የሚል ፈሊጥ ከእንግዲህ እንደማይሰራ የሚናገሩት አቶ ደመቀ፣ የአፈፃፀም ችግር የሚባሉ ሰበቦችም ከእንግዲህ ቦታ የላቸውም ብለዋል፡፡

በግጭቶች እጃቸው ያለባቸው ማናቸውም አካላት በህግ እንደሚጠየቁ የተናገሩት አቶ ደመቀ ይህን የሚያጠጠናና አጣርቶ የሚያቀርብ ግብረ ኃይል መቋቋሙንም አስረድተዋል፡፡

ሁሉም ኢትዮጵያውያን ተከባብረውና መብታቸው ተጠብቆ የሚኖርባት ስርዓት መገንባት እንደሚያስፈልግም በመግለጫቸው አስረድተዋል፡፡በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስ መምህር አቶ ቻላቸው ታረቀኝ እንደሚሉት ደግሞ እተሰበሰቡ መምከሩ ጥሩ ቢሆንም ወደ ተግባር ካልተቀየረ ግን አሁንም የሚመጣ ለውጥ የለም ይላሉ፡፡

ትናንት በባሕር ዳር በተካሄደው ውይይት ከኢፌዲሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ በተጨማሪ የኢፌዲሪ ጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ጀነራል ሳዕረ መኮንን ፣ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ዶ/ር አምባቸው መኮንንና ሌሎች ከፍተኛ የክልልና የፌደራል መንግስት የፖለቲካ አመራሮች፣ የፀጥታና የመረጃ አገልግሎት ኃላፊዎች ተገኝተዋል ፡፡

ዓለምነው መኮንን

ነጋሽ መሐመድ

እሸቴ በቀለ