የናይጀሪያ የአይሮፕላን አደጋ
ማክሰኞ፣ ግንቦት 28 2004
ሀኪም ቤቶች(ሆስፒታሎች) የሟቾቹን ማንነት በማጣራት ላይ ናቸው። እስካሁን ማንነታቸው ከተለየው 40 ሟቾች መካከል፣ የካናዳ እና የቻይና ዜጎች ጭምር እንደሚገኙበት ተገልጿል። አውሮፕላኑ ሌጎስ አየር ማረፊያ ለመድረስ ሲቃረብ፣ በምን ምክንያት ሊከሰከስ እንደቻለ ፣ እስካሁን የሚታወቅ ነገር የለም። የጀርመን ዜና ወኪል ዴ ፔ አ አሁን በመጨረሻ እንዳስታወቀው፣ የናይጀሪያ በረራ ባለሥልጣን መሥሪያ ቤት አደጋ የደረሰበት አውሮፕላን ባለቤት የሆነውን የዳና አውሮፕላን መሥመር የሥራ ፈቃድን ነጥቋል።
ለምንድን ነው አፍሪቃ ውስጥ በአይሮፕላን መብረር አደገኛ የሆነው?
ሁለት የአይሮፕላን አደጋ በአፍሪቃዊቷ ክፍለ አለም በጥቂት ቀናት ውስጥ መሆኑ ነው። ቅዳሜ ምሽት እንዲሁ ጋና ውስጥ አንድ የአጭነት ማጓጓዣ አይሮፕላን የማረፊያ መንገዱን ስቶ ከአንድ መንገደኛ ካሳፈረ አውቶቡስ ጋ ተጋጭቶ ቢያንስ 10 ሰዎች መሞታቸው ተነግሯል።
ምንም እንኳን ከአደጋው የተረፉ የማግኘት እድሉ ጠባብ ቢሆንም በተቻላቸው አቅም ለመርዳት ይሞክራሉ። የዳና ኤር አየር መንገድ የነበረው እና ከአቡዳ ተነስቶ ሌጎስ ሊያርፍ ትንሽ ሲቀረው ትናንት የተከሰከሰው አይሮፕላን ጠቅላላ ተሳፋሪዎች ህይወት አልፏል። አይሮፕላኑ በመኖሪያ አቅራቢያም ስለወደቀ ሌሎች ሟቾች ይገኙበታል። አይሮፕላኑ እንዴት አድርጎ በመኖሪያው አካባቢ እንደወደቀ አንዲት የአካባቢው ነዋሪ እንዲህ ይገልፁታል« አይሮፕላኑ ዝቅ ብሎ ነበር የሚበረው። ሊያርፍ የሚፈልግ ይመስል ነበር። ከዚያም ወዲያውኑ አይሮፕላኑ እንደተከሰከሰ ተመለከትን። »
ሌሎች የአካባቢው ነዋሪዎች እንደገለፁት እሳቱን ለማጥፋት ትልቅ ችግር ነበር። በቂ ውሃ አልነበረም። አደጋው ከደረሰ ከሶስት ሰአታት በኋላም የናይጄሪያ የእሳት አደጋ ተከላካዮች እሳቱን ለማጥፋት አዳግቷቸው ነበር። የናይጄሪያ የበረራ ጉዳዮች ሚኒስትር ወ/ሮ እስቴላ ስለ አደጋው በሰጡት ማብራሪያ እንዲህ ነበር ያሉት።
« የናይጀሪያ ፌዴራል መንግሥት አደጋው የደረሰበትን ምክንያት ለማወቅ እና ተመሳሳይ አደጋ እንዳይደገም ለማከላከል ሰፊ ምርመራ ያካሂዳል። አደጋው የደረሰበትን ምክንያት ቅድም እንዳልኩት ገና አላወቅንም። ሊያርፍ አሥራ አንድ ወደ አሥራ ሰባት ኪሎሜትር ያህል ሲቀረው ነበር የርዳታ ጥሪ ያሰሙት። ይህን ነው እስካሁን የምናውቀው።
ከደረሰው የአይሮፕላን አደጋ በኋላ የናይጄሪያው ፕሬዚዳንት ጉድላክ ጆናታን የ3 ቀናት ብሄራዊ የሀዘን ቀን አውጀዋል። የሌጎስ ከንቲባ ባባቱንዴ ፋሾላ በአደጋው ስፍራ ተገኝተው ስለተሰማቸው ሀዘን ሲገልፁ፤ «ሀዘኑን በአንድ ጊዜ ለመቀበል ቀላል አይደለም። ለመኖር የሚታገሉ ተራ ዜጎች ናቸው በሚያሳዝን እና ባልተጠበቀ ሁኔታ ህይወታቸው ያለፈው። ቤተሰቦች፣ ፓይለቶች እና ባለደረቦቻቸው፣ የወጣት ናይጄሪያውን ህይወት በጠቅላላው በመቀፅበት ተቀጭቷል። እጅግ በጣም የሚያስደነግጥ እና የሚያሳምም አጋጣሚ ነው።»
አፍሪቃ ውስጥ በአይሮፕላን መብረርን ምን አደገኛ እንደሚያደርገው የጀርመኑ የበረራ ትምህርት ቤት ኃላፊ ዚግፍሪድ ኒዴክ ሲያብራሩ፤
« በአሁኑ ጊዜ ትልቁ ችግር አፍሪቃ ውስጥ የበረራ መቆጣጠሪያው ነው። ያም ማለት በአብራሪዎቹ መካከል እና በአይሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ መስመር መሪዎች መካከል ያለ ግንኙነት ማለት ነው። የአውሮፓ አይሮፕላን አብራሪዎች የዚያም ሲሉ የራሳቸውን የውስጥ የራዲዮ መገናኛ ይጠቀማሉ፤ ሁልጊዜ ሌሎች አይሮፕላኖች ያሉበትን ለማረጋገጥ። ይህም የአለም አቀፍ የበረራ ድርጅቶች የሚመክሩት ነው።»
ልደት አበበ
ተክሌ የኋላ