የተጠርጣሪ እስረኞቹ በዋስ መፈታት
ማክሰኞ፣ ነሐሴ 13 2006ወ/ሪት ወይንሸት ሞላ የሰማያዊ ፓርቲ የብሄራዊ ምክርቤት አባል ነች።በፓርቲው የሴቶች ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ ውስጥ በንቃት የምትሳተፈውና በሙሉ ጊዜ አደራጅነት የምታገለግለው ወጣት በፖለቲከኛነቷ ዘልቃ መሪ የመሆን ህልም አላት። እንደ ፖለቲከኛነቷ ዓመት የዘለቀውን የኢትዮጵያሙስሊሞችን ተቃውሞ ሐምሌ 11/2006 ዓ.ም. በአንዋር መስጊድ አካባቢ ተገኝታ ለመከታተል ከውሳኔ ደርሳለች። በእለቱ የነበረውን ሁኔታ ተከታትላ ግን በሰላም ወደ ቤቷ አልተመለሰችም።
ወ/ሪት ወይንሸት ሞላና የአዲስ ጉዳይ መጽሔት ፎቶ ጋዜጠኛ አዚዛ መሐመድን ጨምሮ ሐምሌ 11/2006 ዓ.ም. ከአንዋር መስጊድ አካባቢ በጸጥታ ሃይሎች ቁጥጥር ስር ውለው የነበሩ ሰዎች በተፈጠረው ግጭት ውስጥ ተሳትፎ አድርጋችኋል በሚል ተጠርጥረው ነበር።
ወ/ሪት ወይንሸት ሞላ ፓርቲያችን ካሉት ንቁ እንስት ተሳታፊዎች መካከል አንዷ ናት ሲሉ የተናገሩት የሰማያዊ ፓርቲ ምክትል ሊቀ-መንበር አቶ ስለሺ ፈይሳ በተጠረጠረችበት ወንጀል የምርመራ ሂደቱ ተጠናቆ ክስ አለመመስረቱን ተናግረዋል።
በተጠቀሰዉ ዕለት በአንዋር መስጊድ በተፈጠረው ግጭት ተጠርጥራ በእስር ላይ የነበረችውንና ከወ/ሪት ወይንሸት ሞላ ጋር በዋስ የተፈታችውን የአዲስ ጉዳይ መጽሔት ፎቶ ጋዜጠኛ የአዚዛ መሐመድን አስተያየት በዚህ ዘገባ ለማካታት ያደረግንው ጥረት አልተሳካም። በዚሁ አንዋር መስጊድ ተፈጥሮ ነበር በተባለው ግጭት ተሳትፈዋል በሚል ተጠርጥረው በእስር ላይ የነበሩ አራት የፖሊሶች በዋስ መለቀቃቸውን የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል።
እሸቴ በቀለ
ነጋሽ መሐመድ