የተቀዛቀዘው የቻይና ኢኮኖሚ እና የአፍሪቃውያኑ ድንጋጤ
ረቡዕ፣ የካቲት 9 2008ከአዲስ አበባ አብዛኞቹ የውስጥ ለውስጥ መንገዶችና በቅርቡ ሥራ የጀመረው ቀላል የባቡር ትራንስፖርት ከቻይና በተገኙ የረጅም ጊዜ ብድሮች የተገነቡ እየተገነቡ የሚገኙም ናቸው። ከአዲስ አበባ አዳማ የተገነባውን ዘመናዊ የፍጥነት መንገድ ጨምሮ የኢትዮጵያን ከተሞች እና ክልሎች እርስ በርስ የሚያገናኙት ረዣዥም መንገዶች ግንባታ ውስጥም የቻይና ባንኮች በገንዘብ፤ የግንባታ ኩባንያዎች እና ባለሙያዎች እጅ አለበት።
የቻይና እድገት ግን እንደወትሮው አይመስልም። ለሶስት አስርት አመታት ከፍተኛ እድገት ያስመዘገበችው እና በዓለም ኢኮኖሚ አዲስ ገበያ እና የተፈጥሮ ሐብት ፍለጋ ወደ አፍሪቃ ያተኮረው ቻይና የኢኮኖሚ መቀዛቀዝ ገጥሟታል። የአገሪቱ የአክሲዮን ገበያ እና የውጭ ምንዛሪ ግብይትም መረጋጋት አይታይበትም። በጎርጎሮሳዊው 2015 ዓ.ም. የቻይና ኢኮኖሚ የአገሪቱ መንግስት ካስቀመጠው አማካኝ 7 በመቶ እድገት ማስመዝገብ አልቻለም። ያለፈው ዓመት የ6.9 በመቶ እድገት ከቻይና ጋር የጠበቀ የንግድ ግንኙነት ላላቸው ያደጉት አገሮች ብቻ ሳይሆን ለአፍሪቃውያኑም አሳሳቢ ሆኗል።
የኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናት አሁንም በቻይና ባንኮች እና መዋዕለ ንዋይ ላይ ከፍተኛ መተማመን ይታይባቸዋል። ባለሥልጣናቱ በዓለም 2ኛ ጠንካራ ኢኮኖሚ ባለቤት የሆነችው ቻይና በኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ግንባታው ውስጥ ጠንካራ ሚና እንዲኖራት ይሻሉ። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም ባለፈው ጥቅምት ወር መቀመጫውን ለንደን ላደረገው ፋይናንሺያል ታይምስ ጋዜጣ «ከዚህ የበለጠ መዋዕለ ንዋይ ወደ ኢትዮጵያ እንደሚፈስ እጠብቃለሁ።» ሲሉ ነግረውታል። ይህ የኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን የሌሎች በርካታ የአፍሪቃ አገራትም ፍላጎት ነው። ይሁንና ለአፍሪቃውያኑ እንደ ፍላጎታቸው አልሰመረም። በጎርጎሮሳዊው 2015 ዓ.ም. ቻይና ከአፍሪቃ የንግድ አጋሮቿ የገዛችው ምርት እና ጥሬ እቃ ከቀደመው ዓመት በ40 በመቶ አሽቆልቁሏል። ዝርዝሩን ከድምፅ ዘገባዉ ያድምጡ።
እሸቴ በቀለ
ኂሩት መለሰ