1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የተማሪዎች ግጭት በአክሱም ዩኒቨርሲቲ

ረቡዕ፣ ግንቦት 28 2011

በአክሱም ዩኒቨርሲቲ በተፈጠረ ሁከት የአንድ ተማሪ ሕይወት ማለፉና ሌሎች ሰባት ተማሪዎች መጎዳታቸውን ዩኒቨርሲቲውና የዓይን እማኞች ገለፁ። ዩኒቨርሲቲው ዛሬ ባወጣው የሐዘን መግለጫ በ27 10 2011 በዩኒቨርሲቲው በተፈጠረ ሁከት ዮሐንስ ማስረሻ የተባለ የአክሱም ዩኒቨርሲቲ የ2ተኛ ዓመት የመካኒካል ኢንጅነሪንግ ተማሪ ሕይወት ማለፉን ገልጿል፡፡

https://p.dw.com/p/3JuI6
Äthiopien Axum-Universität in der Region Tigray
ምስል DW/M. Hailesilassie

«የአንድ ተማሪ ሕይወት አልፏል»

የአክሱም ዩኒቨርሲቲ ምክትል ፕሬዝደንት ዶክተር ኪሮስ ጉዑሽ እንደነገሩን የትላንቱ ክስተት መነሻ ምክንያት በሀገሪቱ የተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች እየታየ ካለው ግጭት ጋር የተያያዘ መሆኑ በመግለፅ በድርጊቱ ላይ ተሳተፉ የተባሉ አካላት እንደተያዙና የቀሩትም ለመያዝ እየተሠራ መሆኑን ለዶቼ ቨለ DW ገልፀዋል። የተፈጠረውን ሁከት ለማብረድ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት አባላት እና ፌደራል ፖሊስ ጣልቃ መግባታቸውን የገለፁልን ምክትል ፕሬዝደንቱ በዛሬው ዕለትም ተማሪዎች የማረጋጋት ሥራ እየተሠራ ነው ብለዋል።
በሁከቱ ጉዳት የደረሳቸው ተማሪዎች በአሁኑ ወቅት በአክሱም ዩኒቨርሲቲ ሪፈራል ሆስፒታል ሕክምና እየተደረገላቸው መሆኑ ሰምተናል። ከጉዳዩ ጋር ተያይዞ መግለጫ ያወጣው የትግራይ ክልል መንግሥት ኮምኒኬሽን ቢሮ በዩኒቨርሲቲው የተፈጠረው ነገር በማውገዝ  ወንጀለኞች ለሕግ እንዲቀርቡ እንደሚሠራ ገልፅዋል።  የትግራይ ክልል ምክትል ርእሰ መስተዳድር ከጉዳዩ ጋር ተያይዞ ዛሬ ከሰዓት መግለጫ እንደሚሰጡ ሰምተናል። የትናንቱ የአክሱም ዩኒቨርሲቲ ክስተት  "ማንነትን  መሠረት ያደረገ ጥቃት" በማለት የሚወገዝ ተግባር መሆኑን የትግራይ ክልል ምክትል ርእሰ መስተዳድር  ዶክተር ደብረፅዮን  ገብረሚካኤል መግለፃቸውን ከጥቂት ደቂቃዎች በፊት ዘጋቢያችን ሚሊዮን በላከልን ዜና አመልክቷል። ምክትል ርእሰ መስተዳድሩ ዛሬ አመሻሹ ላይ በሰጡት ጋዜጣዊ  መግለጫ  ድርጊቱን  የፈፀሙትን  ወንጀለኞች  የክልሉ  መንግሥት አድኖ  ለሕግ  እንደሚያቀርባቸውም ገልጸዋል።  ዝርዝሩን የመቀሌው ዘጋቢያችን ሚሊዮን ኃይለ ሥላሴ ልኮልናል።

ሚሊዮን ኃይለ ሥላሴ

ሸዋዬ ለገሠ

ማንተጋፍቶት ስለሺ