1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የብሄራዊ መንግስት ምስረታ በማዕከላይ አፍሪቃዊቱ ሬፑብሊክ

ቅዳሜ፣ ጥር 16 2001

የማዕከላይ አፍሪቃዊቱ ሬፑብሊክ ፕሬዚደንት ፍራንስዋ ቦዚዜ የብሄራዊ አንድነት መንግስት ለማቋቋም የገቡትን ቃል ገሀድ ለማድረግ ባለፈው እሁድ የሀገራቸውን መንግስት በተው አዲስ መንግስት መሰረቱ።

https://p.dw.com/p/Gf5k
ፕሬዚደንት ፍሮንስዋ ቦዚዜ
ፕሬዚደንት ፍሮንስዋ ቦዚዜምስል AP

የማዕከላይ አፍሪቃዊቱ ሬፑብሊክ ፕሬዚደንት ፍራንስዋ ቦዚዜ የብሄራዊ አንድነት መንግስት ለማቋቋም የገቡትን ቃል ገሀድ ለማድረግ ባለፈው እሁድ የሀገራቸውን መንግስት በትነው አዲስ መንግስት መሰረቱ። ከአንድ ዓመት በፊት ተቋቁሞ የነበረው የቀድሞው መንግስት ጠቅላይ ሚንስትር ፎስተን አሮንዥ ቱዋዴራ ብዙም ለውጥ ያልታየበትን አዲሱን መንግስት እንዲመሩ ፕሬዚደንቱ መሾማቸውን የቀድሞው መንግስት ባለስልጣን ፊደል ንጓንቺካ አስታውቀዋል። ለዚሁ የፕሬዚደንቱ ውሳኔ ምክንያት ያሉዋቸውን ነጥቦች እንዲህ ዘርዝረዋቸዋል።

« ጠቅላይ ሚንስትሩ በአንዱ ዓመት የስልጣን ዘመናቸው ችሎታቸውን አስመስክረዋል።ደሞዝ በጊዜው እየተከፈለ ነው። የጡረታ አበልም እንዲሁ። በሙስና አንጻርም ትግሉ ተጀምሮዋል። ባጠቃላይ ብዙዎች ቱዋዴራ የጠቅላይ ሚንስትርነቱን ስልጣን እንዲይዙ በመፈለጋቸው ስልጣኑ ተረጋግጦላቸዋል። »

ይሁንና፡ በአዲሱ መንግስት ውስጥ ያን ያህል ለውጥ ባለመታየቱ፡ ባለፈው ታህሳስ ወር አራት ሚልዮን ህዝብ በሚኖርባት ማዕከላይ አፍሪቃዊቱ ሬፑብሊክ ዘላቂ ሰላም ለማውረድ በሚቻልበት ዘዴ ላይ በተመድ ደጋፊነት በተካሄደው የአስራ ሁለት ቀናት ስብሰባ የተሳተፉት የተቃውሞና ያማጽያን ቡድኖች ቅር ተሰኝተዋል። የቱዋዴራ ድጋሚ በጠቅላይ ሚንስትርነት መሾም ከጦር ኃይሉና ካንዳንል ያማጽያን ቡድን ድጋፍ ማግኘቱን ያማጽያኑ የዩ ኤፍ ዲ አር ቡድን ቃል አቀባይ ግሬቡየር ጃሚል አመልክተዋል።

« በሀገራችን በቂ የልማቱ ስራ ቀጥሎዋል። ሰላምም እየመጣ ነው። ውይይቱም በመካሄድ ላይ ይገኛል። ይህ ሁሉ ሊሆን የቻለው በጠቅላይ ሚንስትር ቱዋዴራ ጥረት ነው። »

የተቃውሞና ያማጽያን ቡድኖች ከታህሳሱ ውይይት በኋላ በአዲሱ መንግስትእ ውስጥ ሰፊ ተሳትፎ እንደሚያገኙ ነበር ተሳፋ ያደረጉት። ነገር ግን በአዲሱ መንግስት ውስጥ አሁንም ብዙውን ስልጣን የያዙት ያው የቀድሞው መንግስት አባላት ናቸው። ፕሬዚደንቱም ቁልፉን የመከላከያ ሚንስትርነትን ስልጣን አሁን እንደያዙ ይገኛሉ። ባጣቃላይ ሲታይ ከሰላሳ ሁለቱ የአዲሱ መንግስት ሚንስቴሮች መካከል ሁለቱ ብቻ ናቸው በዓማጽያኑ ቡድን አባላት የተያዙት።

በታህሳሱ ውይይት ሁለት መቶ የመንግስት፡ የተቃውሞና ያማጽያን ቡድኖች ተወካዮች ተካፋዮች ነበሩ። ፕሬዚደንት ፍሮንስዋ ቦዚዜ እአአ በ 2003 ዓም በመፈንቅለ መንግስት ከስልጣን ያወረዱዋቸውና ካለፉት አምስት ዓመታት ወዲህ በግዞት ከሚኖሩባት ቶጎ ወደ ትውልድ ሀገራቸው በመመለስ ከተቀናቃኛቸው ጋር ስብሰባ ማካሄዳ?ቸው ለውይይቱ ልዩ ትርጓሜ ሰጥቶታል።

በታህሳሱ ስምምነት መሰረት አሁን የተቋቋመው አዲሱ መንግስት እአአ በ ዓም በሀገሪቱ ጠቅላላ ምርጫ እስኪካሄድ ድረስ በስልጣን እንዲቆይ ተወስኖዋል። ከዚህ በተጨማሪም በርካታ ኤኮኖሚያዊ ዘርፎች ቁጥጥር እንዲደረግባቸው፡ የቀድሞ ተዋጊዎችም የጦር መሳሪያ ትጥቃቸውን እንዲፈቱ እና የሀቅና የዕርቀ ሰላም ኮሚሽን እንዲቋቋም በስምምነቱ ላይ ሀሳብ ቀርቦዋል። በግዙፍ የዩሬንየምና የአልማዝ ማዕድን ንጣፍ የታደለችው ማዕከላይ አፍሪቃዊቱ ሬፑብሊክ በሀገርዋ ለብዙ ዓመታት የተካሄደውን ውዝግብ ለማብቃትና መረጋጋት ለማስፈን ባላት ፍላጎት ተነሳስታ በ 2007 እና በ2008 ዓም መካከል በጋቦን ሸምጋይነት ከዓማጽያኑ ቡድኖች ጋር አራት የሰላም ስምምነቶችን ተፈራርማለች።

AT,HM

Quelle: RTR, DW