ሐሙስ፣ መጋቢት 28 2009
ይህን ጉዳይ ሲከታተል የነበረዉ የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን በትናንትናዉ እለት በአደጋው የተጎዱ እስረኞችን ቁጥርና የወደመ ንብረትን በገንዘብ መጠን የያዘ ዘገባ ለህዝብ ተወካዮች ምክርቤት ለህግ፣ ለፍትህና አስተዳደር ቋም ኮምቴ አስረክቧል።
በእስር ቤቱ የእሳት ቃጠሎዉ ከመነሳቱ በፊት ከፍተኛ «እሩምታ እና ረብሻ» እንደነበረ የመንግስት መገናኛ ብዙሃን ዘገባዉን ጠቅሶ ዘግበዋል። እስር ቤት መግባት የሌለባቸዉ እንደ «ላይተርና ለቃጠሎ የሚዳርጉ ቁሳቁሶች» መታየታቸዉም ዘገባዉ አክሎበታል። የቃጠሎው መንሴኤም በከፍተኛ ወንጀል ተጠርጥረው የፍርድ ሂደታቸዉን የሚከታተሉ እስረኞች እሳቱን «ሆን ብሎ እንደሎከሱ» ዘገባዉ ጠቅሶ በዚህም አደጋ የ23 ሰዉ ህይወት እንዳለፈና 15 ሚልዮን ብር የሚያወጣም ነብረት እንደወደመ ጠቅሷል። ከሞቱት 23 ሰዎች መካከል 21 ዱ በጭስ ታፍነዉ ህይወታቸዉ እንዳለፈና ሁለቱ ደግሞ «ሊያመልጡ ሲሉ» በተቶከሰባቸዉ ጥይት እንደሞቱ ዘገባዉ ያብራራል።
የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ዘገባን እንዴት ይመለከቱታል? ብለንም የህዝብ አስተያያት ጠይቀን ነበር። ጉዳዩን በቅርብ የሚከታተሉ በድምፅ አስተያየታቸዉን ሰጥተውናል። ከነዚህም ዉስጥ የአዳማ ነዋሪ መሆናቸዉን የተናገሩት ግን ስማቸዉ ለጊዜዉ እንዳይገለፅ የጠየቁን ግለሰብ «ዘገባዉ የሚያሳፍር» ነዉ» ይላሉ።
በዶይቼ ቬሌ የዋትስፕ ገጽ ላይ የጽሁፍ መልዕክት ካደረሱን ሌላ አንድ የአዲስ አበባ ነዋሪ በቂሊንጦ እስረኞችን ወደ ፍርድ ቤት የሚያመላልስ ወዳጃቸዉ ጉዳዩን አስመልክቶ ያጫወታቸዉን አጋርተዉናል። ግለሰቡ በሰጡን መረጃ መሰረት «እሳቱን እያጠፉ ባሉ እስረኞች ላይ ካላይና ከታች አጋዚዎች «የጥይት እሩምታ» እንደከፈቱባቸዉና በወቅቱ 20 ሰዎች ሞቱ ተብሎ የተገለፀዉ የሟቾን ቁጥር እንደማይቀበሉ በፅሁፋቸዉ ጠቅሰዋል።
የአዳማ ነዋሪ በበኩላቸዉ የኮሚሽኑ ዘገባ «ምንም የሚፈይደው ነገር የለም» ይላሉ።
በመንግስት የኮሙኒኬሼን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤትም በኩል ሆነ በኮሚሽኑም በኩል የበለጠ መረጃ ለማገኘት ያደረግነዉ ሙከራ አልተሳካም።
አዜብ ታደሰ
ዮናስ መርጋ