1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የስፖርት ዘገባ፤ ግንቦት 24 ቀን፣ 2007 ዓ.ም

ማንተጋፍቶት ስለሺማክሰኞ፣ ግንቦት 25 2007

በአውሮጳ ታላላቅ የእግር ኳስ ቡድኖች የአናፊዎች አሸናፊ ፍልሚያ ከእንግሊዝ አርሰናል ሲቀናው የጀርመኑ ቦሩስያ ዶርትሙንድ ለቮልፍስቡርግ እጅ ሰጥቷል። ባርሴሎና አትሌቲኮ ቢልባዎን ድል ነስቶ ዋንጫውን ጨብጧል። ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በዓለም መድረክ በተደጋጋሚ ድል በሚያስመዘግቡበት በአሁኑ ወቅት አትሌቶች ወደ ጀርመን እንዳይመጡ ተከለከሉ ይላሉ።

https://p.dw.com/p/1FaM4
Wolfsburg DFB-Pokal Autokorso Feier Benaglio
ምስል Getty Images/AFP/T. Schwarz

[No title]

በሣምንቱ መገባደጃ ላይ ዩናይትድ ስቴትስ ዩጂን ኦሬጋን ውስጥ በተከናወነ የሩጫ ውድድር ኢትዮጵያውያን ማሸነፋቸው ተዘግቧል። ዮሚፍ ቀጀልቻ በ5000 ሜትር አንደኛ ወጥቷል። የገባበት ሰዓት 13: 10:54 ነበር። በተመሳሳይ ርቀት የሴቶች የሩጫ ፉክክር ገንዘቤ ዲባባ በ14: 19:76 በመግባት በአደኛነት አጠናቃለች። በ800 ሜትር የሩጫ ውድድር ደግሞ ሞሐመ ድ አማን አንደኛ ወጥቷል። የገባበት ሰዓት 1: 44:92።

ኢትዮጵያውያን የማራቶን ሩጫ ተወዳዳሪዎችን በተለይ ጀማሪዎችን ወደ ጀርመን ብሎም አውሮጳ በማስመጣት የተለያዩ ውድድሮች ላይ እንዲሳተፉ በማመቻቸት ለ7 ዓመታት የበጎ ፍቃድ አገልግሎት እንደሰጡ ይናገራሉ። ሹልትስ ሚተንስቫይ ይባላሉ። አብዛኛውን ጊዜ ለውድድር ከኢትዮጵያ የሚያስመጧቸው ሯጮች ልምድ ካላቸው አንስቶ መካከለኛ እና ምንም ልምድ የሌላቸውን እንደሚያካትት ገልጠዋል። ከቅርብ ጊዜ አንስቶ ግን አዲስ አበባ የሚገኘው የጀርመን ኤምባሲ ለአዳዲስ አትሌቶች አውሮጳ ውስጥ በቂ ጊዜ የሚያስቆያቸውን ቪዛ በመከልከሉ ተቸግሬያለሁ ሲሉ ያማርራሉ።

«አዲስ አበባ በሚገኘው የጀርመን ኤምባሲ የቪዛ ክፍል ካለፈው ዓመት አንስቶ አዲስ ኃላፊ ተሹሟል። ከዛን ጊዜ ጀምሮ ቪዛ መስጠት ላይ እጅግ ጥብቅ ሆኗል። ለሯጮች ቪዛ የሚሰጠው የ3 ቀን ብቻ ነው። ያ ደግሞ በጣም ትንሽ ነው። አብዛኞቹ ሯጮች ከ3 እስከ 4 ሣምንታት አንዳንዴም ለ4 ወራት እዚህ በመቆየት በተደጋጋሚ ሮጠው ገንዘብ ማግኘት አለባቸው። ሮጠው በማሸነፍ በሚያገኙት ገንዘብ ደግሞ የአውሮፕላን ቲኬት እና ሌሎች ወጪያቸውን መሸፈን አለባቸው። ያን ከአዲስ አበባ ሆኖ የሚያመቻችላቸው ሰው ገንዘቡ የሆነ ጊዜ እንዲከፈለው ይሻል።»

ኤምባሲው ይሰጣል ያሉት የሦስት ቀን ቪዛ ለሯጮች ከባድ ነው የሚሉት ሹልትስ ሚተንስቫይ አንድ ሯጭ አውሮጳ ውስጥ ከሁኔታዎች ጋር ለመላመድ ቢያንስ የአንድ ሳምንት ጊዜ ያስፈልገዋል ይላሉ። ማንኛውም ስፖርት ከመኪያሄዱ በፊት እና በኋላ ስፖርተኛው በሄደበት ቦታ ከሚያጋጥመው አዲስ የዓየር ጠባይ፣ አዲስ ባህል፣ አዳዲስ ሰዎች ጋር ለመላመድ ጥቂት ቀናት ያስፈልገዋል ሲሉ ይናገራሉ። የባንክ ተቀማጭ፣ መኪና አለያም ቋሚ ጥሪት ማሳየት ያልቻሉት ሯጮች በኤምባሲው ቪዛ ማግኘት ተቸግረዋል ያሉት ሹልትስ ልምድ እና ገንዘብ ያላቸው አትሌቶች ችግር የለባቸውም ብለዋል። ልምድ እና ጥሪት ያላቸውን ሯጮች በተመለከተ ሲናገሩ።

«እነሱ ልምድ እና ተቀማጭ ገንዘብ አላቸው ለእነሱ በጣም ቀላል ነው። የባንክ ደብተራቸውን፣ መኪና አለያም ሌላ ተቀማጭ ጥሪታቸውን ሲያሳዩ ወዲያው ቪዛ ይሰጣቸዋል። እኔ ጥረት አደርግ የነበረው ለአዲስ መጤዎች፣ ገና ልምድ ለሌላቸው ነበር»

የቪዛ ክልከላው ምናልባትም በርካታ ስደተኞች ወደ አውሮጳ በተደጋጋሚ በማቅናታቸው የተነሳ የመጣ ትእዛዝ ሳይሆን አይቀርምም ብለዋል። እሳቸው ለ7 ዓመታት ካስመጧቸው በርካታ ሯጮች መካከል አውሮጳ በመቅረት ጥገኝነት የጠየቀው አንድ ግለሰብ ብቻ መሆኑንም ተናግረዋል። እንዲያ ሆኖ ሳለ ጀርመን በአፍሪቃ አዲስ ፖሊሲዋ መሠረት ስፖርትን ለማጠናከር ከፍተኛ ድጋፍ እንደምታደርግ ብትናገርም ያ ግን ተግባራዊነቱ እምብዛም ነው ሲሉ አማረዋል።

ኢትዮጵያ እና ጀርመን ውስጥ ጉዳዮ ለሚመለከታቸው ግለሰቦች እና ተቋማት በተደጋጋሚ ደብዳቤ ብሰጥም ምላሽ ባለማግኘቴ ከእንግዲህ ለማራቶን ሯጮች በበጎ ፈቃደኝነት የምሰጠውን አገልግሎት አቋርጫለሁ ብለዋል።

አዲስ አበባ ወደሚገኘው የጀርመን ኤምባሲ በመደወል የኤምባሲውን ምላሽ ለማግኘት ያደረግነው ጥረት ለዛሬ አልተሳካም። ወደፊት ኤምባሲው በዚህ ጉዳይ ላይ የሚሰጠው ምላሽ ካለ ለማስተናገድ ዝግጁ መሆናችንን እንገልጣለን።

በጀርመን ቡንደስሊጋ አንደኛ ዲቪዚዮን እና ኹለተኛ ዲቪዚዮን 64 ቡድኖች የሚሳተፉበትና በየዓመቱ የሚከናወነው የጀርመን የፍፃሜ ግጥሚያ ባሳለፍነው ቅዳሜ ተከናውኖ ነበር። ከቦሩስያ ዶርትሙንድን ጋር የተጋጠመው ቮልፍስቡርግ በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ የጀርመን ካፕ የተሰኘውን ዋንጫ ማሸነፍ ችሏል። ቦሩስያ ዶርትሙንድን 3 ለ1 የረታው ቮልፍስቡርግ 30,000 ደጋፊዎቹ ደስታቸውን ለመግለጥ አደባባይ ወጥተዋል።

የቮልፍስቡርግ ተጨዋቾችን የተሸከመው ተሽከርካሪ ከባቡር ጣቢያው ተነስቶ በደጋፊዎች የተጨናነቀውን ሦስት ኪሎ ሜትር ጎዳና ለመዝለቅ ኹለት ሰዓታት እንደፈጀበትም ተገልጧል። ተጨዋቾቹን የተሸከመው የተሽከርካሪ አጀብ ከደጋፊዎች ጋር ፎቶ ግራፍ ለመነሳት በተደጋጋሚ ሲቆምም ተስተውሏል።

ቀዳሚውን ግብ ለቦሩስያ ዶርትሙንድ ያስቆጠረው የጋቦኑ አጥቂ ፒዬር ኤሜሪክ አውባሜዬንግ ቢሆንም፤ በ16 ደቂቃዎች ውስጥ ቮልፍስቡርግ ሦስት ተከታይ ግቦችን በማስቆጠሩ የቦሩስያ ዶርትሙንድ የመጨረሻ ህልም መክኗል። ለቮልፍስቡርግ ሉዊስ ጉስታቮ፣ ኬቪን ደ ብሩይነ እና ባስ ዶስት ግቦቹን አስቆጥረዋል።

በእንግሊዝ የኤፍ ኤ ካፕ ዋንጫ ውድድር አርሰናል አስቶን ቪላን 4 ለዜሮ ድባቅ በመምታት ዋንጫውን አንስቷል። በእለቱ የቺሊው አጥቂ አሌክሲስ ሳንቼስ ድንቅ ብቃቱን ከማሳየቱም ባሻገር በ49ኛው ደቂቃ ላይ ግሩም ግብ አስቆጥሯል። ለአርሰናል ሌሎቹን ግቦች ያስቆጠሩት ቲዎ ዋልኮት፣ ፔር ሜርቴሳከር እና ኦሊቨር ጂሮድ ናቸው። በስፔን ደግሞ ባርሴሎና በአትሌቲ ኮቢልባዎ ላይ የ3 ለ1 ድል ተቀዳጅቷል። በርካታ ጋዜጦች አስማተኛው ብለው የጻፉለት አርጀንቲናዊው ሊዮኔል ሜሲ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር፤ ኔይማርም እኔስ ለምን ይቅርብኝ ብሏል። ሊዮኔል ሜሲ ለባርሴሎና ለ50 ጊዜያት ተሰልፎ ያስቆጠራት 33ኛ ግቡ ቅዳሜ እለት ለፍጻሜ ፍልሚያው በአትሌቲኮ ቢልባዎ መረብ ላይ ያረፈችዋ ናት። የባርሴሎና የዋንጫ ድል ግስጋሴ ቀጥሎ ምናልባት ከፍተናው ደረጃ ላይ የሚጠጋው ጀርመን በርሊን ከተማ ቅዳሜ በሚከናው የሻምፒዮንስ ሊግ ፍፃሜ ይሆናል ተብሎ ተገምቷል። ለሻምፒዮንስ ሊግ ፍፃሜ ባርሴሎና የሚገናኘው ከጣሊያኑ ጁቬንቱስ ጋር ነው።

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ሉዊስ ጉስታቮ
ሉዊስ ጉስታቮምስል Reuters/F. Bensch
የቦሩስያ ዶርትሙንድ አሠልጣኝ የርገን ክሎፕ
የቦሩስያ ዶርትሙንድ አሠልጣኝ የርገን ክሎፕምስል Reuters/M. Sohn
Entwicklerkonferenz Google I/O Google Developers Conference
ምስል Reuters/M. Mac Matzen
የሐምቡርግ ማራቶን
የሐምቡርግ ማራቶንምስል picture-alliance/dpa

ሸዋዬ ለገሰ