የኢትዮጵያውያን ቅሬታ
እሑድ፣ ግንቦት 27 2009የሳዑዲ አረብያ መንግሥት ህገ ወጥ የሚላቸው የውጭ ዜጎች ከሀገሪቱ እንዲወጡ ያስቀመጠው የ3 ወራት የምሕረት ጊዜ ሊያበቃ 23 ቀናት ብቻ ናቸው የቀሩት። መረጃዎች እንደሚያመለክቱት 12 ሚሊዮን የሚደርስ የውጭ ዜጋ በህጋዊ መንገድ እንደሚኖር በሚነገርባት በሳውዲ አረብያ 3 ሚሊዮን ያህል ህገ ወጥ የሚባሉ የውጭ ዜጎች ይገኛሉ። ከመካከላቸው በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩት ኢትዮጵያውያን ናቸው። ይሁን እና ህገወጦች ሊከተልባቸው የሚችለውን ቅጣት ያስቀራል የተባለውን የምሕረት አዋጁን ተጠቅመው ወደ ሀገራቸው የተመለሱም ሆነ ለመመለስ የተዘጋጁት ኢትዮጵያውን ቁጥር ከብዛታቸው ጋር ሲነፃጸር ዝቅተኛ ነው። መጀመሪያ ላይ አነስተኛ የነበረው የተመላሾች ቁጥር ወደ ኋላ ላይ እየጨመረ ቢሄድም በርካቶች ወደ ሀገር ከመመለስ ይልቅ እዚያው መቅረትን የመረጡ ይመስላል። ወደ ሀገራቸው ለመመለስ ከሚፈልጉት መካከልም የጉዞ ወጪያቸውን ለመሸፈን ባለመቻል፣ የጉዞ ሰነድ ለማውጣት በመቸገራቸው እና በሌሎችም ምክንያቶች ከሳዑዲ አረብያ መውጣት እንዳልቻሉ በምሬት የሚናገሩም ጥቂት አይደሉም። ሳዑዲ አረቢያ የሥራ እና የመኖሪያ ሰንድ የሌላቸውን የውጭ ዜጎች ለማስወጣት ያስቀመጠችው ቀነ ገደብ ሊያበቃ አንድ ወር ያህል ሲቀረው የኢትዮጵያ መንግሥት ከሳዑዲ መንግሥት ጋር የተፈራረመው አዲስ የሠራተኛ ሥምሪት ስምምነት ፤ተመላሾች በህጋዊነት ወደ ሳውዲ አረብያ ዳግም እንዲሄዱ ያስችላል ቢባልም ብዙዎች እምነት አልጣሉበትም። የዛሬው እንወያይ በሳዑዲ የምሕረት አዋጅ እና በኢትዮጵያውን ምሬት ላይ ያተኩራል ። በዚህ ጉዳይ ላይ የሚወያዩ አራት እንግዶችን ጋብዘናል። እነርሱም አቶ ፈይሰል አልይ በሳውዲ አረብያ የኢትዮጵያ ኤምባሲ የዳያስፖራ እና የቆንስላ ጉዳዮች ዘርፍ ሃላፊ፣ አቶ ሻውል ጌታሁን በሪያድ የኢትዮጵያ ኮሚኒቲ ማህበር ሊቀ መንበር፣ አቶ ኤልያስ ባሃሮን ሳውዲ አረብያ ውስጥ በግል ስራ የሚተዳደሩ እና ከ35 ዓመት በላይ የኖሩ ኢትዮጵያዊ እንዲሁም ወይዘሮ ቅድስት ኒና በመመለሻ ውጣ ውረድ ሳውዲ አረብያ ውስጥ በመንገላታት ላይ የሚገኙ ኢትዮጵያዊ ናቸው። ውይይቱን የድምጽ ማዕቀፉን በመጫን ማዳመጥ ይችላሉ።
ኂሩት መለሰ
ልደት አበበ