የሩዋንዳ የህግ ማሻሻያዎች፤ የኡጋንዳ ውዝግብ
ቅዳሜ፣ ሐምሌ 13 2011በሩዋንዳ ቅኝ ገዢዎች ከጎርጎሮሳዊው 1885 ጀምሮ ሀገሪቱ ነጻነቷን እስከተቀዳጀችበት 1962 ድረስ በአገሪቱ ዘርግተውት ለነበረው ስርዓት የፍትሐ ብሔር እና የወንጀለኛ መቅጫ ህግን ተግባራዊ አድርገው ነበር። የሚያሳዝነው እና የሚገርመው፣ እንዲያውም የሀገሪቱ የፍትህ ሚኒስትር እንዳሉት "የሚያሳፍረው" ግን ይህን የቅኝ ገዢዎች ሕግ የሩዋንዳ ባለስልጣኖች ሳይቀይሩት እስከ አሁን ድረስ ሲገለገሉበት መቆየታቸው ነው። ባለስልጣናቱ አሁን ወደ አንድ ሺህ የሚጠጉ ሕጎችን ሽረው እና በአዲስ ሕግ ተክተው ለመሥራት ተነስተዋል፡፡
በሩዋንዳ ጉረቤት ኡጋንዳ ተግባራዊ እንዲደረግ የተባለው "የቀረጥ ጭማሪ" ደግሞ በአገሪቱ ውስጥ ውዝግብ አስነስቷል። ኡጋንዳ ተጨማሪ "ቀረጥና ግብር" እንዲከፍሉ ትዕዛዝ ያስተላለፈችው በስልክ ተጠቃሚዎች ላይ ነው፡፡ ከትዕዛዙ ጀርባ የኡጋንዳው ፕሬዝዳንት ዩዌሪ ሙሴቬኒ እንዳሉ ይነገራል። ሙሴቬኒ "ወጣቱ ትውልድ ትምህርት መማሩን ትቶ ጊዜውን በከንቱ በዋትስ አፕ ጉርጎራ እና በአሉባልታ ወሬ ወርቅማ ጊዜውን በከንቱ ያጠፋል" በሚል ሰበብ የቀረጥ ጭማሪውን ማዘዛቸው ተገልጿል።
ኑሮ በተወደደበት በኡጋንዳ "ይህን የቀረጥ ጭማሪ አንከፍልም“ የሚል እንቅስቃሴ በአገሪቱ ላይ ተነስቷል፡፡ታክሲ ነጂዎች እና ተጠቃሚ መንገደኞች፣ ተማሪዎች እና ጋዜጠኞች "አሉባልታ እና ሹክሹክታ ወንጀል አይደለም፣ የመናገር እና ሀሳብ የመግለጽ መብታችን ተረገጠ" ብለው ከሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ጋር አንድ ላይ ሁነው በፕሬዚዳንቱ ላይ ተነስተዋል።
ሙሉ ዘገባውን ለማድመጥ የድምጽ ማዕቀፉን ይጫኑ።
ይልማ ኃይለሚካኤል
ተስፋለም ወልደየስ