1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የምሥራቅ ዩክሬን ህ/ውሳኔና የዩክሬን እጣ

ማክሰኞ፣ ግንቦት 5 2006

ባለፈው እሁድ ምሥራቅ ዩክሬን በተካሄደው ህዝብ ወሳኔ አብላጫ ድምፅ አገኘን ያሉት የምሥራቅ ዩክሬን ተገንጣዮች ትናንት ነፃነታቸውን አውጀዋል ። የተባበሩት መንግስታት ድርጅትም እውቅና እንዲሰጣቸው እየጠየቁ ነው ።

https://p.dw.com/p/1Bz4m
Barrikaden Regionalverwaltung 12.05.2014 Donezk
ምስል DW/K. Oganesian

የኬቭ መንግስትም ሆነ ምዕራባውያን ህዝበ ውሳኔውንም ሆነ ውጤቱን በእጅጉ ተቃውመዋል ። ሩስያ ግን ውጤቱን አከብራለሁ ብላለች ። በዚህ ሳቢያም የአውሮፓ ህብረት በሩስያ ላይ ተጨማሪ ማዕቀቦችን ጥሏል ።ከዩክሬን ለመገንጠል የሚሹ ኃይሎች ነፃነታቸውን አውጀው ከሩስያ ፌደሬሽን ጋር ለመቀላቀል ጥያቄ ኣቅርበው የሩስያን መልስ በመጠባበቅ ላይ ናቸው ። ባለፈው እሁድ ምሥራቅ ዩክሬን ውስጥ በተካሄደው በአወዛጋቢው ከዩክሬን የመነጠል ወይም ያለ መነጠል ህዝበ ውሳኔ ድምፅ ከሰጠው ህዝብ ወደ 90 በመቶ የሚጠጋው ነፃነትን መምረጡን የህዝበ ውሳኔው አደራጅ ኃይሎች አስታውቀዋል ።በነርሱ አባባል ከአካባቢው ነዋሪ 80 በመቶ ያህሉ ድምፅ ሰጥቷል ። የኢንዱስትሪ ክልል ከሆነችው ከዶኔትያስክ ህዝብ 90 በመቶው ከሉሃንስክ ደግሞ 96.2 በመቶው ነፃነት መምረጡን ነው የሩስያ መንግስት ቴሌቪዥን የዘገበው ። ለህዝበ ውሳኔው ከወጡት አንዳንዶቹ እንዳሉት ለነፃነት ድጋፍ የሰጡት ከምዕራባውያን ሃገራት ጫና ለመገላገል ነው ።

Ukraine Referendum Auszählung 11.5.
ምስል Reuters

«ለነፃነታችን እንታገላለን ። ይህን የምናደርገውም ምዕራባውያን የነርሱን ፍላጎት በኛ ላይ በኃይል ለመጫን ስለሚፈልጉ ነው ። በዚህም ምክንያት ለነፃነታችን ሃሳብን በነፃ ለመግለፅ ነፃነት እንዲሁም ለወደፊቱ መብታችን እንታገላለን ። አካባቢው ብዙ ቋንቋዎች ይነገሩበታል ። ምዕራባውያን ግን ይህን አይቀበሉም። እኛ እንደነርሱ እንድንሆን ነው የሚፈልጉት ። እዚህ ብዙ ብሄር ብሄረሰቦች አሉን ። ይህን መረዳት ያስፈልጋል ። ይህን የሚቀበል ከሌለ የርስ በርስ ጦርነት ውስጥ እንገባለን ። ከሩስያ ጋር ስለ ሚኖረው ግንኙነት እኛ የምናደርገው ግፊት አይኖርም ። እንደ ሁኔታው ሩስያ የምትወስነውን እኛም እንቀበለዋለን ካልፈለገች ደግሞ አይሆንም »

ከህዝበ ውሳኔው በፊት ድምፅ አሰጣጡ ለሌላ ጊዜ እንዲገፋ ጠይቃ የነበረው ሩስያ ፣ እሁድ ምሥራቅ ዩክሬን ውስጥ የተካሄደውን ህዝበ ውሳኔ ውጤት እንደምታከብር ትናንት አስታውቃ ውጤቱም በሰላማዊ መንገድ እንዲተገበር አሳስባለች ። ከዚህ በኋላ በበኩሏ ምን ዓይነት እርምጃ እንደምትወስድ ግን አላሳወቀችም ። ከህዝበ ውሳኔው አደራጆች አንዳንዶቹ ቀድሞም የሩስያኛ ቋንቋ ተናጋሪዎች የሆኑት እነዚህ የምሥራቅ ዩክሬን ግዛቶች ከሩስያ ጋር እንዲቀላቀሉ የሚፈልጉ መሆኑንን ነው የሚናገሩት ። ህዝበ ውሳኔውን የዩክሬን ጊዜያዊ መንግሥትም ሆነ ምዕራቡ ዓለም ህገ ወጥ ሲሉ ተቃውመውታል ። የዩክሬን ጊዜያዊ ፕሬዝዳንት ኦሌክሳንድር ቱርቺኖቭ ለሩስያ የሚወግኑ ኃይሎች የጠሩትን ዝህበ ውሳኔ አሸባሪ ባሏቸው ኃይሎች የተፈፀመ ቧልት ነው ያሉት ። በርሳቸው አባባል ህዝበ ውሳኔው በአካባቢው ለተፈፀሙ ግድያዎች አፈናዎች ግጭቶችና ሌሎችም ከባድ ወንጀሎች መሸፋፈኒያነት የተወሰደ እርምጃ ነው ። የአውሮፓ ህብረት አባል ሃገራትም የእሁዱን ህዝበ ውሳኔ እንዳልተቀበሉት ነው ያሳወቁት ። የየሉክስምቡርግ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዦን አሰልቦርን ለሩስያ የሚወግኑት ኃይሎች ያካሄዱትን ህዝበ ውሳኔ አጣጥለዋል ።

Ukraine Donezk Separatistenführer Denis Puschilin
ምስል Reuters

« አዎ እኔ እንደሚመስለኝ እነርሱ የሚጠቀሙበት ህዝበ ውሳኔ የሚለው ቃል ትልቅ ቃል ነው ። በኔ እምነት ህዝበ ውሳኔው የይስሙላ ነው ፣ህጋዊ መሰረት የሌለው በዓለም ዓቀፍ ህግ እይታ ትርጉም የሚሰጠው አይደለም በአጠቃላይ ህገ ወጥና በርግጥም እውቅና ሊሰጠው የማይገባም ነው ። ውጤቱ ምን ያህል ሆነ ምን ተቀባይነት ስለሌለው በዚህ ላይ ሃሳብ በማቅረብ ጊዜ ማጥፋት አያሻም ። »

በምስራቅ ዩክሬን የህዝብ ተወካይ ነን የሚሉት ኃይሎች ግን ለምርጫ የወጣው ህዝብ ቁጥር ከፍተኛነት በራሱ ህዝበ ውሳኔውን ህጋዊ ያደርገዋል ሲሉ ይከራከራሉ ። ከዚህ በኋላም የሩስያን ውሳኔ ብቻ እንደሚጠብቁ ነው ራሱን የዶኔትያስክ ህዝባዊ ሪፐብሊክ የሚለው ቡድን መሪ ዴኒስ ፑሽሊን የተናገሩት ። ባለፉት ቀናት በዩክሬን ወታደሮችና ከዩክሬን እንገንጠል በሚሉ ኃይሎች መካከል በተካሄደ ግጭት በርካታ ሰዎች በተገደሉባት ማሪዩፖል በተባለች ከተማ

በርካቶች ድምፅ ለመስጠት ወጥተዋል ከድምፅ ሰጭዎቹ አንዷ አንዳሉት ይህ በከተማይቱ የተፈጸመው ግፍ ውጤት ነው ። « እዚህ ደም ሲፈስ የማሪዩፑል ህዝብ ለህዝበ ውሳኔው ወጥቶ ድምፅ መስጠት እንዳለበት ተረዳ ። ዛሬ እነዚህን ሁሉ ሰዎች ተመልከቷቸው ። «በጩኽት» ማርዮፖል የዶኔትስክ ህዝባዊ ሪፐብሊክ ደጋፊ ናችሁ ? »

ብራሰልስ ቤልጅየም ውስጥ ትናንት የተሰበሰቡት የ 28ቱ የአውሮፓ ህብረት አባል ሃገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች በዩክሬን የሚሆነውን ሁሉ ታቀነባብራለች

Treffen zwischen Joze Manuel Barroso und Arsenij Jazenjuk in Brüssel 13.05.14
ምስል Reuters

በሚሏት በሩስያ ላይ አራተኛውን ዙር ማዕቀብ ጥለዋል ። በአሁኑ ማዕቀብ ክርሚያ የሚገኙ ሁለት ኩባንያዎች ለመጀመሪያ ጊዜ የእገዳው ሰለባ ሆነዋል ። ሚኒስትሮቹ ሩስያ የቀድሞዋን የዩክሬን ግዛት ክሪምያን የሩስያ ፉደሬሽን አካል ካደረገች በኋላ በሩስያ የተወረሱትን የእነዚህ ኩባንያዎች ሃብትን ንብረት ዝውውር እገዳ ጥለውበታል ። 13 ተጨማሪ ግለሰቦች ሃብት ንብረታቸው እንዳይንቀሳቀስ ና የጉዞ እገዳ እንዲደረግባቸውም ተስማምተዋል ።በዩክሬን ቀውስ ሳቢያ ማዕቀብ የተጣለባቸው ሰዎች ቁጥር አሁን ወደ 61 ከፍ ብሏል ። የሩስያው ኩባንያ ጋዝፕሮም ዩክሬን የእስካሁን የሃይል እዳዋን ካልከፈለች ከ20 ቀናት በኋላ ወደ ዩክሬን የሚልከውን ጋዝ እንደሚያቋርጥ አስጠንቅቋል ። ከዚህም ከዚያም አጣብቂኝ ውስጥ የገባችው የዩክሬን ጊዜያዊ ፕሬዝዳንት ቱርቺኖቭ በሩስያ የተቀነባባረ ያሉት ህዝበ ውሳኔ የዶኔትስክንና የሉሃንስክን ግዛቶች ኤኮኖሚ የዜጎችን ህይወትና ደህንነትለአደጋ የሚያጋልጥ መሆኑን ለዩክሬን ፓርላማ ተናግረዋል ። ቱርቺኖቭ እንደሚሉት እርምጃው በዩክሬን ሁኔታዎች እንዳይረጋጉ የማድረግ ዓላማ ያለው ከመሆኑም በላይ ከ12 ቀናት በኋላ ሊካሄድ የታቀደውን የዩክሬን ምርጫም ለማደናቀፍ ብሎም የዩክሬንን ባለስልጣናት ለመገልበጥ ያለመም ነው ። ምሥራቅ ዩክሬን ውስጥ ከከዩክሬን የመገንጠል ህዝበ ውሳኔ የጠሩት ኃይሎች ስለወደፊቱ እቅዳቸው ሲናገሩ ቱርቺኖቭን ለመተካት በሚካሄደው ምርጫ እንደማይሳተፉ ነው ያሳወቁት ። ቃል አቀባያቸው እንዳስረዱት የሉሃንስክ ሪፐብሊክ አሁን መስርተው በፕሬዝዳንታዊ ምርጫ መሳተፍ እንዳላዋቂ የሚያስቆጥር ነው ። በዚህና በሌሎችም ምክንያቶች አንዳንድ የዩክሬን የፖለቲካ ጉዳዮች ተንታኞች የዩክሬን ምርጫ ላይካሄድ እንደሚችል ከወዲሁ ግምታቸውን እየሰነዘሩ ነው ። የዩክሬን ጉዳዮች አዋቂ ና በጀርመንና በሩስያ ግንኙነት ላይ ጥናታቸውን የሚያካሂዱትሊያና ፊክስ ህዝበ ውሳኔ ለግንቦት 17 2006 ዓም ቀጠሮ በተያዘለት የዩክሬን ምርጫ ላይ ችግሮችን ማስከተሉ እንደማይቀር ተናግረዋል ።

« ከዩክሬን መገንጠል የሚፈልጉት ምሥራቅ ዩክሬን የሚንቀሳቀሱት ኃይሎች መሪ በምርጫው እንደማይካፈሉ አስታውቀዋል ። ያ ማለት ህዝበ ውሳኔው ዩክሬን ይብሱን እንዳትረጋጋ የሚያደርግ ፕሬዝዳንታዊውም ምርጫ እንዳይካሄድ በሰፊው ለመከላከል የተወሰደ ወሳኝ እርምጃ ነው ። ይህ ደግሞ የሞስኮ ዋነኛ ፍላጎት ነው ። ምክንያቱም ምርጫው ከተካሄደ ለሩስያ የሚወግን እጩ ማሸነፉ አጠራጣሪ ነውና ። በርግጥ ይህም ሆኖ ምርጫው ሊካሄድ ይችላል ። ሆኖም የዶኔትስክና የየሉሃንስክ ግዛቶች በምርጫው ካልተካፈሉ በኬቭ መንግሥት ላይ ጠንካራ የህጋዊነት ችግር ያስነሳበታል ። አዲሱ ተመራጭ ፕሬዝዳንትም በዚህ ችግር ውስጥ መውደቃቸው አይቀርም ።»

ይህን ለማስቀረት ይመስላል የዩክሬን መንግሥት አሁንም ቢሆን ምሥራቅ ዩክሬን ከሚገኙ ኃይሎች ጋር ለመወያየት ፈቃደኛ መሆኑን ከመግለፅ ወደ ኋላ አላለም ። ጊዜያዊው የዩክሬን ፕሬዝዳንት ቱርቺኖቭ ለዩክሬን ፓርላማ እንደተናገሩት ምሥራቅ ዩክሬን ከሚገኙ እጃቸው በደም ያልታጠበ ካሏቸውና ዓላማቸውንም በህጋዊ መንገድ ከሚያራምዱ ወገኖች ጋር ውይይቱ እንዲቀጥል ይፈልጋሉ ። በሩስያ ላይ ማዕቀብ የጣለው የአውሮፓ ህብረትም ለዩክሬን ችግር ፖለቲካዊ መፍትሄ በማፈላለግ ጥረቱ እንደሚቀጥል አስታውቋል ። የግንቦት 17ቱ ምርጫ እንዲካሄድ የሚፈልጉት የአውሮፓ ህብረት ጀርመንን የመሳሰሉት አባል ሃገራት ምርጫው እንዲካሄድ የሚያስችሉ ሁኔታዎች በቀሪዎቹ 13 ቀናት እንዲመቻቹ እየጠየቁ ነው ። የአውሮፓ የደህንነትና የትብብር ድርጅት በምህፃሩ የOSCE ባለሥልጣናት በዚህ የዩክሬን ጊዜያዊ መንግሥት በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ከተለያዩ አንጃዎች ጋር የጠረጴዛ ውይይት እንዲያካሂድ ግፊት እያደረገ ነው ።ሆኖም ታጣቂ ቡድኖች ይካፈላሉ ተብሎ በማይጠበቅበት በዚህ ውይይት ላይ እነማን እንደሚሳተፉ በግልፅ አልታወቀም ።

ሂሩት መለሰ

ነጋሽ መሀመድ