አቶ ሲራክ እና የኔዘርላንድስ ህይወታቸው
ማክሰኞ፣ ሚያዝያ 3 2009
ለጥቂት ሳምንታት ታስረው ቢፈቱም ህይወት በኔዘርላንድ ቀላል አልነበረም ። ከዚያም አቶ ሲራክ መጀመሪያ የደች ቋንቋ ከተማሩ በኋላ መደበኛ ትምህርት ቤት ገቡ ። ከፍተኛ ትምህርታቸውንም ቀጥለው የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ያዙ ። ካለፉት 29 ዓመታት አንስቶ በአንድ የመንግሥት መሥሪያ ቤት ውስጥ የማህበራዊ ምክር አገልግሎት ሠራተኛ ናቸው ። ይህን ሥራ የጀመሩትም ትምሕርታቸውን በጨረሱ በአጭር ጊዜ ውስጥ ነበር ። ከአቶ ሲራክ ሥራ ውስጥ ሥራ ፈላጊዎች እና ከሥራ የተባረሩ ሥራ ሊያገኙ የሚችሉበትን መንገድ የሚመራ የምክር አገልግሎት እና ስልጠና መስጠት እንዲሁም መከታተል ይገኙበታል ። አቶ ሲራክ እንደሚሉት መንግሥት ለዜጎቹ ሥራ ለመስጠት የተለያዩ መንገዶችን ይጠቀማል ። ከመካከላቸው አንዱ ርሳቸው በሚሰሩበት መስሪያ ቤት አማካኝነት የሚሰጠው አገልግሎት ነው ። በዚህ ሥራ ላይ ታዲያ ለሀገሩ እንግዳ ለሰዉ ባዳ በነበሩበት የመጀመሪያዎቹ ዓመታት ያግዙ እና ይረዷቸው የነበሩ ኔዘርልናዳዊ ወዳጃቸውን መልሰው ለመርዳት የበቁበትን አጋጣሚ እንደነበር አቶ ሲራክ ያስታውሳሉ ።የቴክኖሎጂው እድገት በመጠቀበት በዚህ ዘመን ፣ከሥራ ፈላጊው፣ ከቴክኖሎጂው ጋር የሚሄድ እውቀት ይጠበቃል ። አቶ ሲራክ ቀድሞ ትምሕርት የማይጠየቅባቸው ዝቅተኛ የሚባሉ ሥራዎች ሳይቀሩ አሁን ኔዘርላንድስ በመሳሰሉ ሀገራት በቀላሉ የሚገኙ አይደሉምይላሉ ። በሌላ በኩል ግን በሀገሪቱ ወደፊት ብዙ የሰው ኃይል የማያስፈልገው የሥራ መስክ መኖሩ አልቀረም ።በአብዛኛዎቹ የአውሮጳ ሀገራት የተሻለ ህይወት ለመምራት ከህብረተሰቡ ጋር ተዋህዶ መኖር ወሳኝ ነው ። ለዚህም የሀገሩን ቋንቋ ባህሉን ታሪኩን አኗኗሩን እና አስተዳደሩን ጠንቅቆ ማወቅ ያስፈልጋል ። ለመሆኑ በኔዘርላንድስ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ምን ያህል ከህብረተሰቡ ጋር ተዋህደዋል ማለት ይቻላል ።ለትውልድ ሀገራቸው ከፍተኛ ፍቅር እንዳላቸው የሚናገሩት አቶ ሲራክ በሙያቸው ሀገራቸውን መርዳት ይፈልጋሉ ። ለሀገራቸው እና ለህዝቧም ብዙ ይመኛሉ ።
ኂሩት መለሰ
ሸዋዬ ለገሠ