የሊቢያ እና የአውሮፓ ህብረት የትብብር ስምምነት
ማክሰኞ፣ ጥር 24 2003ማስታወቂያ
የአፍሪቃ ህብረት አባል የሆነችው ለቢያ እንደ አውሮፓ ህብረት ሁሉ የአፍሪቃን ና የአውሮፓ ህብረትን የጋራ ስልታዊ አጋርነት እንዲሁም በአፍሪቃም ዘላቂ እድገትን ለማስፈን የሚደረገውን ጥረት በተግባር የመተርጎም ፍላጎት ያላት አገር ናት ። ሊቢያ የአካባቢውን እንዲሁም የዓለምን ደህንነት በማስጠበቅ እንዲሁም የፅንፈኞችን መስፋፋት በመግታትና የባህር ትራንስፖርትን በመቆጣጠር ረገድ የምትጫወተው ሚናም ቀላል የሚባል አይደለም ። ከአፍሪቃ በነዳጅ ዘይት ክምችት ቀዳሚውን ስፍራ የምትይዘው 6 ሚሊዮን ህዝብ ያላት ሊቢያ ለአውሮፓ ነዳጅ ዘይት በማቅረብ ሶሶተኛውን ደረጃ የምትይዝ አገር ናት ። የአውሮፓ ህብረት የሊቢያ ቀዳሚ የንግድ አጋር ሲሆን እ.ጎ.አ በ 2009 ዓ.ም ብቻ ከአጠቃላዩ ንግድ 70 በመቶው ከሊቢያ ጋር የተካሄደው ነው ። ሊቢያ ከዚህ ውጭ ወደ አውሮፓ መግባት የሚሹ ስደተኞች ዋነኛ መሸጋገሪያ ድልድይም ናት ። አንዳንድ የአውሮፓ ህብረት አባል ሀገራትም በተናጠል ከሊቢያ ጋር ከስደተኞች ጋር የተያያዙ እና በልዩ ልዩ ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ ስምምነቶች አሏቸው ። ከዛሬ 3 ዓመት አንስቶ በአውሮፓ ህብረትና በሊቢያ የስምምነት ማዕቀፍ ላይ ድርድር እየተካሄደ ነው ። በዚህ ስምምነት ውስጥ ሊቢያ ከአውሮፓ ህብረት የማይፈለጉ ስደተኞችን እንድትቀበል የሚጠይቀው ክፍል ይገኝበታል ። ይህ ሃሳብ ከአውሮፓ ህብረት ፓርላማ በኩል ተቃውሞ ቀርቦበታል ። ስምምነቱን የመረመረው የህብረቱ ፓርላማ አባላት ቡድን ጉዳዩ ለሚመለከተው የአውሮፓ ህብረት ምክር ቤት ይህንና ሌሎች ሊቢያ ማስተካከል አለባት ያላቸውን ጉዳዮች ያካተተ ዘገባ ከሁለት ሳምንት በፊት አቅርቧል ።
ሂሩት መለሰ
ነጋሽ መሀመድ