የሁለት ዓለም ሕይወት እስራኤልና ፍልስጤም
ሐሙስ፣ ጥቅምት 18 2008
ከ3 ሳምንት በፊት አርብ እለት ነበረ መሀመድ የቀኑን የመጀመሪያ ፀሎት መስጊድ ሄዶ ለማድረስ በጠዋት ከቤቱ የወጣው ። አጎቱ እንደተናገረው ምርጥ ልብሶቹን ነበር የለበሰው ።ምንም እንኳን መሀመድ የ19 ዓመት ወጣት ቢሆንም ቀን ላይ ወደ ቤቱ ሳይመለስ ሲቀር ቤተሰቡ መጨነቅ ጀመረ ።ከጥቂት ጊዜያት በኋላ አንድ ወታደር መጥቶ መሀመድ አልጃባሪስ መሞቱን አረዳቸው ።ወታደሩ መሀመድ አንድ እስራኤላዊ ወታደር በቢላዋ ወግቶ ካቆሰለ በኋላ ጭንቅላቱ ላይ በጥይት ተመቶ መገደሉን ነገራቸው ። አጎቱ እንደሚሉት ይህን ያደረገው መሀመድ አንድ ጊዜም ችግር ውስጥ ገብቶ አያውቁም ።እናቱ አይዳ ከቤታቸው ጀርባ ከተሰቀለው የመሀመድ ፎቶ ስር ተቀምጠው ይቆዝማሉ ።
«አዎን ምንም ጥያቄ የለውም ። መሀመድ በአልአስካ መስጊድ ውዝግብ ሰበብ ሰማዕት ሆኗል ።ምክንያቱ ደግሞ መስጊዱን ሲከላከሉ የነበሩ ሴቶች ስለተዋረዱና ስለተደበደቡ ነው ።»
እናቱ በንግግራቸው መሃል ከቁራን አንዳንድ አባባሎችን እየጠቀሱ ሃዘናቸውን ለመርሳት ይሞክራሉ ።በመካከሉ ፈገግ ቢሉም አይናቸው እንባ ማቀርዘዙ አልቀረም ።ፌርስ የተባለው የመሀመድ ታላቅ ወንድም ምድር ቤት የሚገኝ የወንዶች ልጆች መኝታ ቤት እያመለከተ ከአራቱ አልጋዎች አንዱ አሁን ባዶ ሆኗል ሲል ሃዘኑን ይገልፃል ።ፌርስ መሀመድን ወደ እስራኤል ይዞት ሊሄድ ፈልጎ ነበር ።ሥራም አግኝቶለት ነበር ፣መሀመድ ግን አልፈለገም ።
« ወንድሜን ገደሉት ።ከነዚህ ሰዎች ጋር ከአሁን በኋላ አብሬ አልሠራም ። ይህ ሊሆን አይችልም ።በኛ አባባል ፣በኛ ና በነርሱ መካከል ደም አለ ። ከአሁን በኋላ የነርሱን ዓይን ማየት አልችልም ።»
ከአንድ ቀን በፊት ከለሊቱ 9 ሰዓት ወታደሮች መጥተው ቤታቸውን እንደለኩት የመሀመድ አባት ተናግረዋል ። በወቅቱም አዛዡ የነርሱ ቤት ብቻ ተለይቶ ይውደም ወይም ጠቅላላው ህንፃ ይፍረስ ለጊዜው የተናገረው ነገር የለም።እነርሱ እንደሚሉት ቤተሰቡ የሚቀጣው የሌሎች አሸባሪዎችን ቅስም ለመስበር ሲባል ነው ።
ከሄብሮን ወደ እየሩሳሌም በሚወስደው በዮርዳኖስ ወንዝ ምዕራባዊ ዳርቻ መንገድ ላይ በ20 ና በ30 ዎቹ የእድሜ ክልል የሚገኙ ወጣቶች ተሰብስበው «እግዜአብሄር ከኛ ጋር ነው፣አንፈራም » እያሉ ድምፃቸውን ከፍ አድርገው ሲዘምሩና ሲደንሱ ይታያሉ ።ወጣቶቹ ወታደራዊ ሥልጠና ወደሚሰጣቸው ቻጋይ ስታምለር እየሄዱ ነው ። በአጠገባቸው የሚያልፉ ባለመኪናዎች ድጋፋቸውን ለመግለፅ የመኪና ጡሩምባቸውን ከፍ አድርገው ያሰሙ ነበር ። ቻንጋይ «ይህ የአይሁድ መሪት ነው ።ሰላም እንጂ ሽብር አይፈልግም »ሲል ይናገራል ። ፍልስጤማውያን ለምን እንደሚገደሉ ሲጠየቅ ግን ስሜቱ ተቀየረ ።
«ከምርህ ነው ?እኛ ፍልስጤማውያንን ተኮስንባቸው ? በአባባሉ ደንግጬያለሁ ።አንድ ስለት የያዘ ሰው ወደ አንተ ቢመጣ ምን ታደርጋለህ ?እነርሱ ህጻናትን እየገደሉ አንተ ትተኩሱባቸዋላችሁ ትላለህ ። »
በዚያው ሰሞን አንድ ምሽት ላይ እዚያው ሄብሮን በአንድ የፍተሻ ኬላ ላይ ሁለት ፍልስጤማውያን ወጣቶች አንድ እሥራኤላዊ ወታደር በጩቤ ለመውጋት ሲሞክሩ ወታደሩ መጠነኛ ጉዳት ሲደርስበት እነርሱ ደግሞ ተገድለዋል ። ሟቾቹ የ17ና የ15 ዓመት ወጣቶችና የአልጃባሪስ ቤተሰብ አባላት ነበሩ ።
ኂሩት መለሰ
አዜብ ታደሰ