የሁለቱ ሱዳኖች ሥምምነትና ገቢራዊነቱ
ረቡዕ፣ መጋቢት 4 2005
የሰሜን እና የደቡብ ሱዳን ባለሥልጣናት ተቋርጦ የነበረዉ የነዳጅ ዘይት ምርትና ሽያጭ እንዲቀጥል ትናንት ተስማምተዋል።በሥምምነቱ መሠረት ደቡብ ሱዳን በሁለት ሳምንት ዉስጥ ነዳጅ ዘይት ማምረት ትጀምራለች፥ ሠሜን ሱዳን ደግሞ ነዳጅ ዘይቱ ወደ ዉጪ የሚያልፍበትን መሥመርና ወደብ ትከፍታለች።አዲስ አባባ ዉስጥ የሚደራደሩት ባለሥልጣናት ከነዳጅ ዘይት በተጨማሪ ጦራቸዉን ከአዋሳኝ ድንበራቸዉ አካባቢ አርቀዉ ከወታደራዊ እንቅስቃሴ ነፃ ቀጣና ለመመስረትም ተስማምተዋል።ታዛቢዎች እንደሚሉት ሥምምነቱ የሁለቱን ሱዳኖች ጠብ ለማብረድ፥ ምጣኔ ሐብታቸዉን ለመገንባትም ጠቃሚ ነዉ።በተያዘለት ጊዜ ገቢር መሆኑን ግን ብዙዎች ይጠራጠራሉ።ነጋሽ መሐመድ ዝር ዝር ዘገባ አለዉ።
አምና ይኼኔ የዉጊያ ዛቻ-ፉከራ፥ የጠብ-ቁርቁስ እንኪያ ሠላንቲያ ነበር የደራዉ። ዘንድሮ፥ ድርድር፥ እና ሥምምነት።እንደ መነታረኪያ፥ መዛዛቻ፥ መጋጪያዉ ሁሉ የመደራደሪያ፥ መስማሚያ ጉዳዮችም ብዙ ናቸዉ።ከብዙዎቹ ዋና በሚባሉት በሁለቱ ጉዳዮች ሁለቱ ሱዳኖች ተስማምተዋል።ነዳጅ ዘይትና ፀጥታ።
የሁለቱ ሱዳኖች መሪዎች ባለፈዉ መስከረም በፈረሙት ጥቅል ዉል መሠረት በአዋሳኝ ድንበራቸዉ አካባቢ ከወታደራዊ እንቅሰቃሴ ጥብቅ ቀጣና ይመሠርታሉ።የበታች ባለሥልጣኖቻቸዉ በዝርዝር አፈፃፀሙ ላይ ተነጋግራዉ ሁለቱም ሱዳኖች ጦራቸዉን ከአዋሳኝ ድንበራቸዉ አስር-አስር ኪሎ ሜትር ለመሳብ፥ ጦሩን መሳቡን እስከ መጋቢት ማብቂያ ድረስ ለማጠናቀቅ ተስማሙ።አርብ።
«የፀጥታ ሥምምነት የአፈፃፀም ቀመሮች ዉል ተፈራርመዋል።ይሕ ወሳኝ ጉዳይ ነዉ።ወታደሮቻቸዉን ከድንበር አካባቢ ማስወጣታቸዉ ደግሞ በጣም ጠቃሚ።»
ይላሉ ጀርመናዊቷ የምሥራቅ አፍሪቃ የፖለቲካ ጉዳይ አጥኚ ዶክተር አኔተ ቬበረ። በየድንበሩ የሠፈረዉ ጦር ባለፈዉ ሰኞ ድንኳኑን መንቀል፥ምሽጉን መድፈን ሲጀምር አዲስ አበባ ላይ የሁለተኛዉ ትልቅ ሥምምነት ገቢር የሚሆንበት ሥልትና ዕለት ተፈረመ።የነዳጅ ዘይት ምርትና ማስተላለፊያ።
«ሱዳንም ደቡብ ሱዳንም የነዳጅ ዘይት ምርትና ሽያጭን መጀመሩ ለሁለቱም እንደሚጠቅም መገንዘባቸዉ ጥሩ ነዉ።ምክንያቱም ሁለቱም በመጀመሩት የቁጠባ እርምጃ ረጅም ጊዜ መቀጠል አይችሉምና።»
በርግጥም ደቡብ ሱዳን የነዳጅ ማዉጪያ ጉርጓዶችዋን ባለፈዉ ዓመት ጥር ከዘጋች ወዲሕ የአዲሲቱ ሐገር ዘጠና ስምንት በመቶ፥የነባሪይቱ ሱዳንም አርባ-አምስት ከመቶ ገቢ ዜሮ ገብቶ ነበር።በቀን ሰወስት መቶ ሐምሳ ሺሕ በርሚል የሚገመተዉ ነዳጅ ዘይት መመረትና ወደ ዉጪ መላኩ የሁለቱን ሐገራት ምጣኔ ሐብት ለማንሰራራት ጠቃሚ ነዉ።
በሥምምነቱ መሠረት ነዳጅ ዘይት አምራች፥ አጓጓዝና ገዢ ኩባንዮች በሰወስት ሳምንት ዉስጥ ነዳጅ ዘይቱን ማምረትና መሸጥ ይጀምራሉ።ቬቨር ግን በተያዘዉ ጊዜ የታቀደዉን ገቢር ማድረግ አይቻልም ባይናቸዉ።
«እንደሚመስለኝ ቴክኒካዊ አፈፃፀሙ ጊዜ ይጠይቃል።በሠማነዉ መሠረት ቧንቧዎቹ ዳግም ነዳጅ ዘይት እንዲተላለፍባቸዉ ለማድረግ መፅዳት፥ መጠገንና ሌላም ቴክኒካዊ እድሳት ያስፈልጋቸዋል።»
ማራቶኑን ድርድር የሚመሩት የአፍርቃ ሕብረቱ ዋና አደራዳሪ የቀድሞዉ የደቡብ አፍሪቃ ፕሬዝዳት ታቦ ኢምቤኪ የሁለቱ ሱዳኖች ባለሥልጣናት የነዳጅ ዘይት ምርትና ሽያጩን የተፈራረሙበትን ዕለት «የድል ቀን» ይሉታል።
ይሁንና ሱዳኖች ሲስማሙም፥ ሲጣሉም ያሁኑ እና የእስካሁኑ የመጀመሪያቸዉ አይደለም።እንደ ጎርጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር በሁለት ሺሕ አምስት የሱዳን መንግሥትና የያኔዉ የደቡብ ሱዳን ነፃ አዉጪ ጦር/ ንቅናቄ የዛሬዋን ደቡብ ሱዳንን ለነፃነት ያበቃዉን የሠላም ዉል ከተፈራረሙ ወዲሕ ሱዳኖች ሠላም ለማስፈን እየተስማሙ፥ ከመወዛገብ፥ እየተደራደሩ ከመጋጨት፥ እየተፈራረሙ ከመዋጋት ሌላ-ሌላ ታሪክ የላቸዉም።
ያሁኑም ሥምምነት ዶክተር ቬበር እንደሚሉት እንደ ከዚሕ ቀደሞቹ ላለመፍረሱ ዋስትና የለም።
«ሁለቱም ወገኖች ባልተፈቱ በሌሎች ጉዳዮች በተወዛገቡ ቁጥር የነዳጅ ዘይት ምርትና መተላለፊያን እንደ መያዢያ መጠቀማቸዉ አይቀርም።የአብዬ ግዛት የማንነት ጥያቄ፣ ድንበር የመከለልና የማረጋገጡ ጉዳይ መፍትሔ አልተበጀላቸዉም።ሁለቱም ወገኖች በነዚሕ ጉዳዮች የየራሳቸዉን አቋም ለማጠናከር የነዳጅ ዘይት ምርትና መተላለፊያን እንደ መሳሪያ መጠቃማቸዉ አይቀርም።ሥለዚሕ መቼና በምን ምክንያት እንደሚቆም ባይታወቀም ነዳጅ ምርትና መተላለፊያዉ እንደገና የሚቆምበት ብዙ ምክንያቶች ግን አሉ።»
ሁለቱ ሱዳኖች ቢያንስ ላሁኑ መስማማታቸዉ ከግጭት-ጦርነት ዉድመት፥ይልቅ፥ የድርድር ሥምምነት ልማትን መምረጣቸዉን መስካሪ ነዉ።ሁለቱን ወገኖች የሸመገሉ፥ ያግባቡ፥ ያስማማቱ ደግሞ ዶክተር አኔተ ቬበር እንዳሉት አዉሮጳ-አሜሪካኖች አይደሉም።አፍሪቃዉያን-የአፍሪቃ ሕብረት እንጂ።
ነጋሽ መሐመድ
ሒሩት መለሰ