የሀዘን መግለጫ ሰልፍ በአዲስ አበባ እና በፓሪስ
ረቡዕ፣ ሚያዝያ 14 2007እራሱን እስላማዊ መንግሥት (IS) ብሎ የሚጠራዉ ቡድን ሊቢያ ዉስጥ የገደላቸዉን ኢትዮጵያዉያን ዛሬ በብዙ ሺሕ የሚቆጠር የአዲስ አባባ ነዋሪ በሠልፍ አሰባቸዉ።የአዲስ አበባን መስቀል አደባባይ ያጥለቀለቀዉ ሕዝብ ግድያዉን አዉግዞ፤ ሟቾችን ሻማ በማብራትና በሌሎችም ሥርዓቶች ዘክሯቸዋል።መንግሥት ለጠራና ላደራጀዉ ሠልፈኛ ንግግር ያደረጉት ጠቅላይ ሚንስትር ሐይለ ማርያም ደሳለኝ ኢትዮጵያዉያኑን ስደተኞች «ለሞት የዳረጓቸዉ» ያሏቸዉን ደላሎች አዉግዘዋል።ይሁንና አሶስየትድ ፕረስ የተሰኘዉ የአሜሪካ ዜና አገልግሎት እንደዘገበዉ የሐዘን መግለጫ የነበረዉ ሠልፍ መንግሥትን ወደ መቃወምና ቁጣ ተቀይሯል።ሠልፈኛዉ መንግሥትን የሚቃወሙ መፈክሮችና ዉግዘቶች ማሰማት ሲጀምር ፀጥታ አስከባሪዎች ሠልፈኛዉን ለመበተን የሐይል እርምጃ ወስደዋል።ከሠልፈኞች መካከልም በፖሊስ ላይ ድንጋይ የሚወረዉሩ ነበሩ።በግጭቱ ከሠልፈኛዉም ከፖሊስም በርካታ ሰዎች መቁሰላቸዉ ተዘግቧል።በዘገባዉ መሠረት ፖሊስ በርካታ ሰልፈኞችን አስሯል።የቆሰሉና የታሰሩ ሰዎችን ቁጥር የሚጠቁም ዘገባ ግን እስካሁን አልደረሰንም።ይሁንና በፀጥታ አስከባሪዎቹ ርምጃ የቆሰሉ ወጣቶች ወደ ሀኪም ቤት ሲወሰዱ መመልከቱንም ወኪላችን ጌታቸው ተድላ ኃይለ ጊዮርጊስ ገልጾልናል።
ከዛሬ ማርፈጃ ወዲህ በከተማይቱ ያለው ሁኔታ ምን እንደሚመስል፣ ግጭቱ በርድ ብሎ ስለመሆን አለመሆኑ፣ ስለታሰሩት ሰዎችና ስለታሰሩበት ምክንያት ፣ የኢትዮጵያውያኑን መገደል በመቃወም ዛሬ ከአዲስ አበባ ውጪስ ተመሳሳይ ሰልፍ ስለመደረጉ፣ በአሰቃቂ ሁኔታ የተገደሉትን ዜጎች ለማሰብ በሚቀጥሉትስ ቀናት የተያዘ እቅድ ስለመኖር አለመኖሩ ወኪላችን ዮሐንስ ገብረእግዚአብሔር በስልክ ማብራሪያ ሰጥቶናል።
በፓሪስ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንም ግድያውን በመቃወም ትናንት አደባባይ ወጥተው ነበር። ሀይማኖት ጥሩነህ ተከታትላዋለች። ሶስቱንም ዘገባዎች ያድምጡ።
ጌታቸው ተድላ ኃይለ ጊዮርጊስ
ዮሐንስ ገብረእግዚአብሔር
ሀይማኖት ጥሩነህ
አርያም ተክሌ
ሂሩት መለሰ