ዞን 9 ጦማርያን የ «ሲፒጄን» ሽልማት ተቀበሉ
ረቡዕ፣ ኅዳር 15 2008ማስታወቂያ
የዓለም አቀፍ የፕሬስ ነፃነት ሽልማቱ ከዞን 9 ጦማርያን በተጨማሪ ለሶርያ ፤ ለማሌዥያና ለፓራጓይ ጋዜጠኞችም ተበርክቶአል። ሽልማቱ ከጎርጎርዮሳዊ 1991 ዓ,ም ጀምሮ በ « ሲፒጄ » አማካኝነት መሰጠት የጀመረ ሲሆን ዓላማዉ ጋዜጠኞች በዘገባቸዉ ምክንያት ለሚደርስባቸዉ እንግልት እዉቅና ለመስጠት መሆኑም ታዉቋል። መቀመጫዉን በኒዩርክ ያደረገዉ ለጋዜጠኞች የሚሟገተዉ ድርጅት «ሲፒጄ» በአካሄደዉ የሽልማት ሥነ-ስርዓት ላይ በአሜሪካን ሀገር ስደት ላይ የሚገኙት የዞን ዘጠኝ አባላት ሶልያና ሽመልስና ፤ እንዳልካቸዉ ኃይለሚካኤል ተገኝተዉ ድርጅቱ ያበረከተላቸዉን ሽልማት ተቀብለዋል።
በሽልማቱ ሥነ-ስርዓት ላይ የተገኘዉ እንዳልካቸዉ ኃይለሚካኤል ሽልማቱ አስደሳችም አሳዛኝም መሆኑን ገልጾአል። የሲፒጄ የአፍሪቃ ፕሮግራሞች ዳይሪክተር ሱቫለንታይን በበኩላቸዉ ጦማሪዎቹ ለሽልማት የበቁት ፈታኝ በሆነ ሁኔታ ዉስጥም ሆነዉ ኃሳባቸዉን ለማስተላለፍ ላደረጉት ጥረት እዉቅና ለመስጠት መሆኑን ተናግረዋል። የዋሽንግተኑ ዘጋቢያችን ናትናኤል ደበበ የዞን ዘጠኝ አባልና የሲፒጄን የአፍሪቃ ፕሮግራሞች ዳይሪክተር አነጋግሮ ዘገባ ልኮልናል።
ናትናኤል ደበበ
አዜብ ታደሰ