ኮሮናን የመከላከል እርምጃዎች
እሑድ፣ መጋቢት 20 2012ከወራት በፊት እምብዛም ትኩረት ያልተሰጠው የኮሮና ወረርሽኝ ባለጸጋ ድሀ፣ ጉልበተኛ ደካማ ሊቅ መሀይም ሳይል በዓለማችን በአስደንጋጭ ሁኔታ በፍጥነት መሰራጨቱንና የሰዎችን ሕይወት ማጥፋቱን ቀጥሏል።በቴክኖሎጂ ምጥቀት ወደ አንድ መንደርነት በተቀየረችው ዓለም ኮሮና ነግሶ እንቅስቃሴን ገቶ ሰዎችን አስጨንቆና አስጠብቦ ዓለምን እያዳረሰ ነው።ሲከሰት የቻይና ችግር ብቻ ተደርጎ ችላ የተባለው ኮሮና አሁን በተለየ አውሮጳ እና ዩናይትድ ስቴትስን ብዙ ዋጋ እያስከፈለ ነው። ተህዋሲው በቴክኖሎጂ በሃብት እና በእውቀት የተሻለ ደረጃ ላይ ይገኛሉ የሚባሉትን የበለጸጉ ሃገራት ገመና አደባባይ አስጥቷል። ለሌላ ይተርፉ የነበሩ ሃገራት ዛሬ በህክምና መሳሪያዎች እና በቁሳቁስ እጥረት እየተቸገሩ ነው።ከመካከላቸው ልዕለ ኃያሏ አሜሪካ፣ከአውሮጳ ኢጣልያ እንዲሁም ከእስያ ኢራን ይገኙበታል።በአሁኑ ጊዜ ኮሮና በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ ተጽእኖ ያላሳደረበት መንግሥትም ሆነ ሰው የለም ማለት ይቻላል።መንግሥታት የበሽታውን ሥርጭት ለመቀነስ ልዩ ልዩ ገደቦችን እና ክልከላዎችን ተግባራዊ እያደረጉ ነው። ድንበር የዘጉ የአውሮፕላን በረራ ያቆሙ ከቤት አትውጡ አንስቶ ህብረተሰቡ አካላዊ ርቀትን እንዲጠበቅ ትዕዛዝ ያሳለፉ በርካታ ሃገሮች ናቸው። በኮሮና ተህዋሲ የተያዙ ሰዎች በተገኙባት በኢትዮጵያም ካለፈው ሳምንት መጨረሻ አንስቶ የተለያዩ የጥንቃቄ እርምጃዎች ተወስደዋል። የኢትዮጵያ ዝግጅት እና የበሽታው ሥርጭት የዛሬው እንወያይ የሚያተኩርባቸው ጉዳዮች ናቸው።በዚህ ርዕስ ላይ የሚወያዩ አራት እንግዶችን ጋብዘናል። እነርሱም ከኢትዮጵያ ዶክተር ፈይሳ ረጋሳ በኢትዮጵያ ማህበራዊ ጤና ተቋም የዓለም አቀፍ ጤና ደንብ የኢትዮጵያ ተወካይ፣ዶክተር አንዳርጋቸው ኩምሳ በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር መድኃኒት የተላመደ ቲቢ ክፍል ከፍተኛ ተመራማሪ ዶክተር ታየ ንጉሴ የማህበራዊ ሳይንስ ባለሞያ እና ዶክተር ጸጋዬ ደግነህ በስራ ባህል እና የአስተሳሰብ ለውጥ ላይ የሚሰሩ እና ስለ ኮሮና የሚጽፉ የምጣኔ ሃብት ባለሞያ ከጀርመን ናቸው። ሙሉውን ውይይት ለመከታተል የድምጽ ማዕቀፉን ይጫኑ
ኂሩት መለሰ
ልደት አበበ