ኬን ሳሮ ዊዋን እና አጋሮቹን ማስታወስ
ማክሰኞ፣ ጥቅምት 30 2008በጀነራል ሳኒ ኣባቻ በተመራው የናይጀሪያ መንግስት በ1995 በስቅላት የተቀጡት ናይጀሪያዊው ደራሲ እና የተፈጥሮ አካባቢ ተሟጋቹ ኬን ሳሮ ዊዋ በጎርጎሪዮሳዊው 1989 «ለኦጎኒ ህዝብ ኅልውና የሚታገል ንቅናቄ» የተሰኘውን ድርጅት አቋቁሙ። ድርጅታቸው የነዳጅ አምራች ኩባንያ፣ ሼል በነዳጅ ዘይት በታደለው እና የኦጎኒ ብሄር መኖሪያ በሆነው የኒዠር ደለል ያደረሰውን ግዙፍ ያካባቢ ብክለትን እና ላካባቢው ትኩረት ባልሰጠው የቀድሞው ጀነራል ሳኒ አባቻ አምባገነን መንግስት አንጻር ትግላቸውን ቀጠሉ። የነዳጅ ዘይት አምራች ኩባንያው ሼል ከብዙ ዓመታት ወዲህ የበከለውን ለምለሙን የኦጎኒ ምድር እንዲያጸዳ፣ መንግሥትም ያካባቢውን ሕዝብ ከነዳጅ ዘይቱ ሽያጭ ገቢ ተጠቃሚ እንዲያደርግ እና ለኦጎኒ ብሄርም ሰፊ ራስ ገዝ አስተዳደር እንዲሰጠው በሰላማዊ መንገድ መጠየቅ ያዙ። ይህንኑ ትግላቸውንም እንዴት እንደሚያካሂዱ ያኔ ኬን ሳሮ ዊዋ ሲያስረዱ፣ « ታላቋዋ ኦጎኒ፣ የተከበረች መሬት፣ ታላቋዋ ኦጎን በሃብት የተሞላች መሬት፣ የኦጎኒን ሕዝብ አስጠነቅቃለሁ። እኛ የምንታገለዉ በገጀራ አይደለም፣ የኛ ትግል በዕውቀት እና በሰላመዊ ዘዴ የሚካሄድ ነው። ምንም ደም መፍሰስ የለበትም።»
እንደ ጎርጎሪዮሳዊው የዘመን ቀመር በ1993 ወደ 300,000 የኦጎኒ ሕዝብ በነዳጅ ኩባንያዉ እና በጄነራል ኣባቻ መንግስት አንጻር ሰላማዊ ተቃዉሞ በማካሄድ፣ ኬን ሳሮ ዊዋ የሕዝባቸውን ቅሬታ ስናገሩ፣ «ዓለም የኦጎኒ ሕዝብ እንዴት እንደታገለ አይቶዋል። መንግስት እየሰረቀን መሆኑን እና ሼልም እኛን እና አካባቢያችንን እያወደመ መሆኑን አይቶታል።»
ኬን ሳሮ ዊዋ ለዚሁ ሰላማዊ ትግላቸው በ1994 የኖቤል ሰላም ተሸላሚ ሆነዋል። ድርጅታቸው የቀጠለው ሰላማዊ እና ግዙፍ ተቃውሞ ሼል አካባቢውን ለቆ እንደወጣ አስገድዷል። ይሁን እንጅ ፣ የሼልን ለቆ መውጣት ያልፈለገው የጀነራል ሳኒ አባቻ ወታደራዊ መንግሥት በሰላማዊ ተቃዋሚዎች አንጻር ግዙፍ የኃይል ርምጃ ከመውሰዱም ሌላ የኦጎኒን ግዛት በቁጥጥር ስር አዋለ።
ይህን ተከትሎ የሰላማዊ ተቃውሞ መሪ ኬን ሳሮ ዊዋ በወታደራዊው መንግሥት በተደጋጋሚ ለእስር ተዳርገው ነበር፣ ከዚያ ግንቦት 1994 ከስምንት «ለኦጎኒ ህዝብ ኅልውና የሚታገል ንቅናቄ» አጋሮቻቸው ጋር አራት የኦጎኒ ብሄር ኃላፊዎችን ገድላችኋል በሚል ክስ እንደገና ታሰሩ። ወታደራዊው መንግሥት ባቋቋመው የጦር ፍርድ ቤት ለታይታ በተካሄደ ችሎት በስቅላት እንዲቀጡ ተበየነባቸው። የኬን ወንድም ኦውንስ ችሎቱ በተካሄደበት በዚያን ጊዜ ከሼል ኃላፊ ጋር ተገናኝተው ወንድማቸው እና ሌሎቹ ተከሳሾች ነፃ ሊወጡ ስለሚችሉበት ጉዳይ አነጋግረው እንደነበር ለመገናኛ ብዙኃን እንድህ ስል ገልጸዋል፣ « ወንድሜ እና ሌሎች አብረውት የሰሩት ነፃ ሊለቀቁ ስለሚችሉበት ጉዳይ ጠየቅሁዋቸው። እነሱን መልቀቅ አዳጋች እና እንደማይቻል ነው የነገሩኝ። ይህ ይሆን ዘንድ ከ«ለኦጎኒ ህዝብ ኅልውና ከሚታገል ንቅናቄ» በጎ ፈቃደኝነት ያስፈልጋል። እኔም ያ በጎ ፈቃድ ማለት ምን እንደሆነ ጠየኩ፣ ድርጅቱ በሼል አንጻር የጀመረውን ዘመቻ ማቆም እንደሚገባው ነገሩኝ።»
የኖቤል ሰላም ተሸላሚው ኬን ሳሮ ዊዋ እና የአጋሮቹ በስቅላት መቀጣት ዓለም አቀፍ ቁጣ እና ውግዘት ነበር የተፈራረቀበት። በኦጎኒላንድ እና በሌሎች የኒዠር ደለል አካባቢዎች ኬን ሳሮ ዊዋ እና ስምንቱ አጋሮቹ ከተሰቀሉ ከ20 ዓመት በኋላም እንደቀጠለ ነው።
ቢርጊት ሞርገንራት
መርጋ ዮናስ
አርያም ተክሌ