ካንሰርን የመካለክል ስልት
ማክሰኞ፣ ግንቦት 20 2005የዓለም ጤና ድርጅት እንደሚለዉ የሳንባ፤ የሆድ፤ የጉበት፤ የጡት ካንሰር በየዓመቱ በካንሰር ምክንያት ህይወታቸዉን ለሚያጡ ሰዎች ዋነኛ ምክንያቶች ናቸዉ። ሰዎች በተለይ ለጡት ካንሰር የሚያጋልጡ ምልክቶችን አስቀድመዉ ሊከታተሉና ሊያዉቁ እንደሚችሉ የዘርፉ ሃኪሞች የሚጠቁሙት።
እናቷ የጡን ካንሰር ሲያሰቃያቸዉ ቢቆይም በማህጸን ካንሰር ነዉ ህይወታቸዉን ያጡት። አያቷም እንዲሁ የማህጸን ካንሰር ተጠቂ እንደነበሩ የቤተሰቧ የጤና የኋላ ታሪክ ያመለክታል። ይህ ከፍተኛ ስጋት ያሳደረባት የፊልም ተዋናይ የአንጀሊ ጆሊ ለዚህ ጉዳይ ከፍተኛ ትኩረት መስጠቷ አያስደንቅም። በተደጋጋሚ ያካሄደችዉ ምርመራ እሷምጋ ያለዉን ጥርጣሬ አባባሰዉ። ባለፈዉ ግንቦት ስድስት ቀን 2005ዓ,ም ለኒዉ ዮርክ ታይምስ በጻፈችዉ እንደጠቀሰችዉ ሃኪሞች በጡት ካንሰር የመያዝ እድሏ 87 በመቶ እንደሆነ በማህጸን ካንሰርም እንዲሁ 50 በመቶ እንደደረሰ ገልጸዉላታል። ስለዚህም «አደጋዉን በተቻለኝ አቅም ለመከላከል ርምጃ ለመዉሰድ ወሰንኩ።» ትላለች። አንጀሊና። አንጀሊና እናቷን እና አያቷን ያሳጣት የጡት እና የማህጸን ካንሰር በሳምንቱ መጨረሻ ደግሞ አክስቷንም ነጥቋታል።
አክስቷ ከማረፋቸዉ አስቀድሞ በባለቤታቸዉ አማካኝነት እንደገለፁት አንጀሊና ጆሊ በጡት ካንሰር የመያዝ እድሏ 87 በመቶ መሆኑን ያመለከታት ምርመራ በዘር ብራካ 1 የተሰኘዉን የዚህኑ ችግር አመላካች እንደወረሰች ሲረጋገጥ ያን ለመከላከል የወሰደችዉን ርምጃ አወድሰዋል። ቢያንስ እንደሰዉ በአቅሟ ለበሽታዉ የመጋለጥ እድሏን ለመቀነስ ሞክራለች። እናት አያቷን የጡትና የማህጸን ካንሰር እንደነጠቃት ታዉቃለች እና የእሷንም ሕይወት ሊቀማ የማድባቱን ምልክት በምርመራ ደረሰችበት። እናም ሁለት ጡቶቿ በቀዶ ጥገና ተወገዱ። ለዉበት በሚል ቅብጠት ተፈጥሮ የሰጣቸዉ አካላቸዉን እንደቅርጻቅርጽ እያስቆረጡ እንደሚቀጥሉት አይደለም ዉሳኔዋ። ይህቺን የልጆች እናት ለዚህ ቆራጥ ርምጃ ያደፋፈራት እናቷን የቀማት ትናንት ደግሞ አክስቷን የወሰደባት ምህረት የለሹ በሽታ ካንሰር ነዉ።
ሌሎች ግን የእሷን ፈለግ መከተል መጀመራቸዉ እየተነገረ ነዉ። ይህ ያሰጋቸዉ ባለሙያዎችም በጉዳዩ ይወያዩበት ጀምረዋል። የዘርፉ የህክምና ባለሙያ የሆኑት ዶክተር ቦጋለ ሰሎሞን አሜሪካዊቱ የፊልም ተዋናይ የወሰደችዉ ርምጃ በህክምና ምርመራ የተደገፈ ከሆነ ተገቢ እና የሚመከር ነዉ ይላሉ። እንዲያም ሆኖ ግን በአንድ ቤተሰብ በካንሰር የተጠቃ ሰዉ መኖሩ ሌላዉ የቤተሰብ አካልንም የግድ ያዳርሳል ማለት እንዳልሆነ፤ ካንሰርን ለመከላከል ለምሳሌ አንጀሊና የወሰደችዉ ርምጃም ከጡት ካንሰር ቢታደጋት በጥቅሉ በሌላ የካንሰር ዓይነት ከመጠቃት ሊያድናት ይችላል ማለት እንዳይደለም ባለሙያዉ ይጠቁማሉ።
ሸዋዬ ለገሠ
ሂሩት መለሰ