ኦብነግ ሰላምና ልማትን መረጋገጥ እንደሚሰራ ገለፀ
ሐሙስ፣ መጋቢት 26 2011ማስታወቂያ
ከሦስት አስርት ዓመታት በላይ በኤርትራ መሽጎ ለኦጋዴን ነፃነት ሲታገል የቆየው የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃነት ግንባር/ኦብነግ በጠቅላይ ሚንስትር ዶ/ር አብይ አህመድ የመጣውን ለውጥ ተከትሎ ከመንግስት ጋር ባደረገው ስምምነት ሀገር ቤት ከገባ ወራት አስቆጥሯል። የሶማሌ ክልልን በመምራት ላይ የሚገኘው እና በአዲሱ ስያሜው የሶማሌ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ / ሶዴፓ ባካሄደው የሰሞኑ ድርጅታዊ ጉባዔ ላይ በተጋባዥነት ተገኝቶ ነበር። የግንባሩ የኮሚዩኒኬሽን ኃላፊ አቶ ሁሴን ሙር በፓርቲው የማጠቃለያ መድረክ ላይ ግምባሩ ለክልሉ ሰላምና ልማት መረጋገጥ እንደሚሰራ ተናግረዋል ። በጠቅላይ ሚንስትሩ የተጀመረው ለውጥ ወደ ሀገራቸው እንዲገቡም ሆነ ፖለቲካዊ ዓላማችንን በሰላማዊ መንገድ እንድናራምድ አድርጎናል ያሉት ሀላፊው ከመንግስት ጋር የገቡትን ስምምነት ተግባራዊ እንደሚያደርጉ ገልፀዋል። ግንባሩ ወደ ሀገር ውስጥ መግባቱን ተከትሎ ከአንድ ሺ ስድስት መቶ በላይ የሚሆኑ ወታደሮቹን የተሀድሶ ስልጠና እንዲወስዱ ወደ ማሰልጠኛ ማስገባቱንና ከስልጠናው በኃላ በሶማሌ ክልል የፀጥታ መዋቅር ውስጥ ገብተው እንደሚሰሩ መግለፁ የሚታወስ ነው።
መሳይ ተክሉ
አዜብ ታደሰ
ሸዋዬ ለገሠ