1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

እሳተ-ገሞራ፤ በረራና መንገደኞች፣

ረቡዕ፣ ሚያዝያ 20 2002

አውሮፓ ውስጥ፣ ከሚያዝያ 7 አንስቶ በማገርሸት በተትጎለጎለው የአይስላንድ እሳተ-ገሞራ ሳቢያ፣ ከአንድ ሳምንት ላላነሰ ጊዜ በአውሮፓ የታላላቅ አኤሮፕላን ማረፊያ ጣቢያዎች መዘጋትም ሆነ፣ የበረራዎች መሠረዝ፣

https://p.dw.com/p/N8xg
ምስል picture alliance / dpa

ዓለም አቀፉ የአየር መጓጓዣ (ትራንስፖርት)ማኅበር እንዳስታወቀው፣የ 1,7 ቢሊዮን ዶላር ኪሣራ ነው ያደረሰው። በአመዛኙ የተጎዱት የአውሮፓ አየር መንገድ ኩባንያዎች ናቸው። የአውሮፓው ኅብረት ኮሚሽን የማጓጓዣ ጉዳይ ከፍተኛ ባለሥልጣን ሲም ካላስ ግን 2,5 ቢሊዮን ዩውሮ ማለት የ 3,3 ቢሊዮን ዶላር ክሥረት በማጋጠሙ አባል መንግሥታቱ፤ አስቸኳይ የማገገሚያ ድጎማ እንዲሰጡ ተጠይቀዋል ሲሉ አስታውቀዋል።

ባለፈው መጋቢት ፣ የሰሜን አሜሪካና የአውሮፓ የአየር መንገድ ኩባንያዎች፣ ማለፊያ የገቢ እመርታ ካሳዩ በኋላ ነበረ የሚያዝያው ያልታሰበ ኪሣራ ያጋጠመው። በቺሌ በደረሰው የእሳተ ገሞራ ፍንዳታ ሳቢያ የላቲን አሜሪካ አየር መንገድ ድርጅቶች ገቢ ባለፈው መጋቢት እጅግ ማሽቆልቆሉ ተመልክቷል። በአንጻሩ፣ የመካከለኛው ምሥራቅ አየር መንገዶች ገቢያቸው በአመዛኙ ከፍ ሲል የአፍሪቃ የአየር መንገድ ኩባንያዎችም የማገገም ምልክት እንዳሳዩ ታውቋል።

ስለእሳተ-ገሞራ ጢስና ዐመድ ምንነት እንዲሁም በበረራ ላይ ሊያስከትል ስለሚችለው ሳንክ፣ ባለፈው ሳምንት መሳይ መኮንን አንድ ባለሙያ በማነጋገር ሳይንሳዊ መረጃ ማቅረቡ ይታወሳል።

የእሳተ-ገሞራ ፍንዳታ ጢስና ዐመድ አደጋ፣ በማንኛውም ጊዜ ሊያጋጥም እንደማይችል ዋስትና የለም። አሁን እንደተጠቀሰው፣ የአየር መንገድ ኩባንያዎች ስለደረሰባቸው ኪሣራ በሰፊው ሲነገር እንሰማለን። የገቢ ምንጭ የሆኑላቸው ደንበኞቻቸው ያልታሰበ መጉላላት ሲያጋጥማቸው እምብዛም ግምት ውስጥ አለመግባቱ ደግሞ አያስገርምም አይባልም።

ተክሌ የኋላ

ሒሩት መለሰ