ኤድስ እና የወጣቱ ግንዛቤ
ዓርብ፣ ኅዳር 27 2006ባለፈው እሁድ የዓለም የኤድስ ቀን ታስቦ ሲውል የተመድ በመረጃ ነው ቀኑን አስቦ የዋለው። እንደ ድርጅቱ ከሆነ በአዳጊ ሀገራት በኤድስ በሽታ የሚሞተው ወጣት ቁጥር እየጨመረ ነው። የተባበሩት መንግስታት የህፃናት መርጃ ድርጅት በምህፃሩ UNICEF እኢአ በ2005 ዓም በኤድስ የሞተውን ቁጥር ከ2012 ጋር ሲያነፃፅር ከ71000 ወደ 110 000 ሺ ከፍ ብሏል። UNICEF ወጣት ብሎ በመዘርዝሩ ያሰፈራቸው ከ10-19 የእድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙትን ሲሆን በጠቅላላው ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ የሚገኝ ወጣቶች በዓለም ዙሪያ 2,1 ሚሊዮን እንደሚደርሱ ይገመታል። አብዛኛዎቹ የኤድስ ህሙማን የተመዘገቡባቸው ሀገራት ከሰሀራ በስተደቡብ የሚገኙ ሀገራት ናቸው።
«መቅድም ኢትዮጵያ ናሽናል አሶሴሽን » በአዲስ አበባ የሚገኝ በተለይ ለኤድስ ህሙማን ድጋፍ የሚሰጥ ማህበር ነው። ከዚህም ሌላ ስለበሽታው እርስ በርስ የሚማከሩ በተለያየ የእድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ አባል እና በጎ ፍቃደኞች በማህበሩ ይገኛሉ። ቤተልሔም 18 ዓመቷ ነው። HIV ቫይረስ በደሙ የሚገኝ ሰው ደፍሯት እሷም የኤድስ በሽተኛ ሆናለች። በራስ መተማመኗ እንዳይቀንስ ስትል ነው ማህበሩን የተቀላቀለች። እሷና መሰለቿ በአንድ ክበብ ውስጥ የተለያየ ትምህርት ያገኛሉ እነሱም ለሌሎች ትምህርት ያካፍላሉ። ቤተልሔም ለሌሎች ቫይረሱ በደማቸው ለማይገኝ ወጣቶች ስለ HIV ቫይረስ ስትገልፅላቸው ያላቸው ግንዛቤ እና አቀባበል ምን እንደሚመስል አጫውታናለች።
ቤተልሔም እና ሌሎቹ የክበቡ አባላት ስብሰባ እና ዝግጅት ሲኖር ጥሪ የተደረገላቸው ቦታ እየተገኙ ትምህርት ይሰጣሉ። ከማህበሩ ውጪ በትምህርት ቤት ደረጃ ቤተልሔም እና ሌሎች ተማሪዎች ኤድስን በሚመለከት የሚያገኙት ግንዛቤ መጠን ግን ያን ያህል በቂ አይደለም።
መምህር አባቴነህ አዛገ በምዕራብ ጎጃም ዞን ደምበጫ ከተማ መሰናዶ ትምህርት ቤት የስነ ዜጋ እና ስነ ምግባር እንዲሁም የፊዚክስ መምህር ናቸው። ተማሪውን ስለ HIV ቫይረስ ግንዛቤ የማስጨበጡ ስራ በትምህርት ቤት ደረጃ እንደቀነሰ ነው የታዘቡት። እንደ የተመድ ዘገባ ከነፍሰ ጡር ወደ ልጅ ቫይረሱ የሚተላለፍበት ሁኔታ ከበፊት ጋር ሲነፃፀር በከፍተኛ ሁኔታ ቀንሷል። ባለፈው አመት 260 000 የሚሆኑ ህፃናት ቫይረሱ ሲተላለፍባቸው ከሰባት ዓመት በፊት ከነበረው 540 000 አሀዝ ጋር ሲነፃፀር ቁጥሩ ከእጥፍ በላይ ቀንሷል። ይሁንና በወጣቱ ዘንድ ያለውን የግንዛቤ ጉድለት ለማሻሻል አሁንም ድረስ በገፋት ይኖርበታል። መምህር አባቴነህም በዚህ ይስማማሉ።
በየሀገራቱ ስለ ኤድስ ግንዛቤ የመስጠቱ ተግባር እንዲቀጠል ሲመከር ዮናይትድ ስቴትስ ደግሞ 100 ሚሊዮን ዶላር በኤድስ ላይ ምርምር እንዲደረግ ለሚቀጥሉት 3 ዓመታት ባጀት መፍቀዷን ትናንት አስታውቃለች። ዘገባውን በድምፅ ያገኙታል።
ልደት አበበ
ተክሌ የኋላ