1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኢራን ዩራኒየም ማብላላት እንደምትጀምር አስታወቀች

እሑድ፣ ሰኔ 30 2011

ኢራን ከአራት ዓመታት በፊት ከአምስቱ ልዕለ-ኃያላን ጋር ከተስማማችበት ገደብ በላይ ዩራኒየም ማብላላት እንደምትጀምር አስታወቀች። እርምጃው ከዚህ ቀደም በኢራን ላይ ተጥለው የነበሩ ማዕቀቦችን ወደ ነበሩበት ይመልሳል። «በየትኛውም መጠን ዩራኒየም ለማብላላት ሙሉ በሙሉ ዝግጁ ነን» ብለዋል የኢራን አቶሚክ ኃይል ቃል አቀባይ ቤሕሮዝ ካማልቫንዲ።

https://p.dw.com/p/3Li5r
Iran PK Regierungssprecher zu Atomabkommen
ምስል Irna

ኢራን ከአራት ዓመታት በፊት ከአምስቱ ልዕለ-ኃያላን ጋር ከተስማማችበት ገደብ በላይ ዩራኒየም ማብላላት እንደምትጀምር አስታወቀች። እርምጃው ከዚህ ቀደም በኢራን ላይ ተጥለው የነበሩ ማዕቀቦችን ወደ ነበሩበት ይመልሳል። በዛሬው ዕለት አንድ ከፍተኛ የኢራን ባለሥልጣን በአገሪቱ ብሔራዊ የቴሌቭዥን ጣቢያ በቀጥታ በተላለፈ ንግግራቸው የአውሮፓ አገራት ኢራንን ከአሜሪካ ማዕቀቦች መጠበቅ እስካልቻሉ ድረስ አገራቸው በየ60 ቀናቱ በስምምነቱ የገባችበትን ግዴታ እየቀነሰች እንደምትሔድ ተናግረዋል። 
«በየትኛውም መጠን ዩራኒየም ለማብላላት ሙሉ በሙሉ ዝግጁ ነን» ያሉት የኢራን አቶሚክ ኃይል ቃል አቀባይ ቤሕሮዝ ካማልቫንዲ በስምምነቱ መሰረት ለኢራን የተቀመጠውን ዩራኒየም የማብላላት መጠን አገራቸው በዛሬው ዕለት እንደምትሻገር ገልጸዋል።
የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት ኤማኑዌል ማክሮ ስምምነቱን ይጥሳል ያሉትን የኢራን እርምጃ አውግዘዋል። ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የሚመሯት አሜሪካ በኢራን የኑክሌር ጦር መሳሪያ ግንባታ ላይ ከተፈረመው ስምምነት ቀድማ መውጣቷ አይዘነጋም። የኢራንን ውሳኔ «እጅግ አደገኛ» ያሉት የእስራኤሉ ጠቅላይ ምኒስትር ቤኒያሚን ኔታንያሁ በበኩላቸው የአውሮፓ አገራት የቅጣት ማዕቀብ ሊጥሉ ይገባል ብለዋል። የኦራኑ ውጭ ጉዳይ ምኒትስር መሐመድ ዣቫድ ዛሪፍ ስምምነቱን የፈረሙ የአውሮፓ አገሮች ቃላቸውን ካከበሩ ኢራን ውሳኔዋን ልትቀለብስ እንደምትችል ገልጸዋል። 

Iran Teheran PK zur Urananreicherung
ምስል picture-alliance/dpa/E. Noroozi

እሸቴ በቀለ

አዜብ ታደሰ