አፍጋኒስታንና ሐሚድ ካርዛይ
ዓርብ፣ መጋቢት 26 2006ት በሥልጣን ላይ ከቆዩ በኋላ ነበረ ፤ አፍጋኒስታንን መልሶ መገንባት ይችላሉ ተብለው ተስፋ የተጣለባቸው ሐሚድ ካርሳይ ብቅ ያሉት። ከፓሽቱ ብሔር የአንድ ታዋቂ ቤተሰብ ባልደረባ የሆኑት ካርሳይ እ ጎ አ በ ታኅሳስ ወር 2001 ዓ ም፤ ቦን አቅራቢያ ፔተርስበርግ ቤተ መንግሥት በተካሄደው የአፍጋኒስታን ጉባዔ፣ የሽግግሩ መንግሥት ፕሬዚዳንት እንዲሆኑ መመረጣቸው የሚታወስ ነው።
ካርሳይ፣ በአፍጋኒስታን የእርስ- በርስ ውጊያ እጃቸውን ደም ካላስነኩት ጥቂት ቤተሰቦች መካከል አንዱ፤ እንዲሁም ከዩናይትድ ስቴትስ ጋር ጥሩ ግንኙነት ያላቸው ሆነው ነው በወቅቱ የተገኙት። ከዚያን ጊዜ አንስቶ የሆነው ሆኖ የሥልጣኑን እርፍ እንደጨበጡ ነው የቆዩት። የ 12 ዓመቱ የካርሳይ የሥልጣን ዘመን እንዴት ነው የሚገመገመው? ዋስላት ሃስራት- ናዚሚ ያቀረበውን ዘገባ ተክሌ የኋላ እንደሚከተለው ያቀርበዋል።
የአፍጋኒስታኑ መሪ ሐሚድ ካርዛይ፣ ባለፉት 10 ዓመታት ገደማ ምንድን ነው አከናወኑ የሚባለው? እርግጥ ነው ካርሳይ በውጭ አመራር ዘይቤአቸው ከፓኪስታን ጋር ጥሩ ግንኑነት መመሥረት አልቻሉም ሙስናናም ለማስወገድ አልበቁም ። በአፍጋኒስታን የፍሪድሪኽ ኤበርት ድርጅትሥራ አስኪያጅ ወ/ሮ አድሪየን ቮልተርስዶርፍ ግን ለየት ያለ አመለካከት አላቸው።
«ከ 10 ዓመት በላይ በአፍጋኒስታን የበላይነቱን ሥልጣን እንደያዙ ለመቆየት የቻሉ ናቸው ።ምናልባት በዓለም ውስጥ ከሁሉም እጅግ ከባዱ የፖለቲካ ሥራ ይህ ነው።»
ብዙ የሥልጣን ሽኩቻ በሚታይበት ሀገር ፣ ይህን ማድረግ መቻል በቀላሉ የሚታይ አይደለም። ካርሳይ እጅግ አስተዋይና ዘዴኛም ናቸው። ለምሳሌ የሄራት ክፍለ ሀገር ገዥ እስማኢል ከፊል ካን፣ ከፊል ነጻ የአገዝዝ ስልት መከተል ሲጀምሩ፣ የካቢኔአቸው አባል ነበረ ያደረጓቸው። የሥልጣኑን ሚዛን እንዲጠበቅ በማድረግ የልማት እርዳታ እንዲገባ አብቅተዋል። በዛ ያሉ ሴት ልጆች ትምህርት ቤት ገብተው መማር የቻሉት ባለፉት 10 ዓመታት ውስጥ ነው። አዳዲስ ዩንቨርስቲዎች ተሠርተዋል የቀድሞዎቹም ታድሰዋል። በዛ ያሉ የራዲዮና ቴሌቭዥን ጣቢያዎችም ተከፍተው ተግባራቸውን በሚያረካ መልኩ ማከናወናቸው አልቀረም።
ያም ሆኖ፤ በመጀመሪያ ማለፊያ ስም የነበራቸው ካርዛይ የምዕራባውያን አሻንጉሊት ናቸው የሚል እምነት ባሳደሩ ወገኖች ዘንድ መጠላታቸው አልቀረም። እ ጎ አ በ2004 በብዙኀኑ ፍላጎት ነበረ ሰፊ ድምፅ አግኝተው ለማሸነፍ የበቁት። በ 2009 ግን በሰፊ የድምፅ ማጭበርበር ተግባር ነው ሥልጣን ላይ ለመቆየት የበቁት። የፀጥታው ይዞታ ደፈረሰ ፣ በአዲሶቹ ታሊባኖች የሚጣለው አደጋ በረከተ። ዩናይትድ ስቴትስም በካርዛይ ላይ የነበራት እምነት ቀነሰ።
ካርዛይ፤ በዩናይትድ ስቴትስ ድጋፍ ሥልጣን ላይ ለመቆናጠጥ መብቃታቸው የታወቀ ነው። ይሁንና በዚህ ዓመት የ NATO ጦር ኃይል አፍጋኒስታንን ሲለቅ፤ ከዩናይትድ ስቴትስ ጋር ስለሚደረግ የፀጥታ አያያዝ ን የሚመለከት ውል ለመፈራረም አለመፈለጋቸው ብዙዎች ታዛቢዎችን አስደምሟል።የአፍጋኒስታን የሰብአዊ መብት ኮሚሽንሊቀመንበር ሲማ ሳማር በበኩላቸው፤ ካርዛይ አያስገርሙም፤ ሁሉን ነገር ያውቃሉ። የሚፈልጉትም በድብቅ መበቀል ነው ማለታቸው ተጠቅሷል። ያም ሆኖ ሙሐመድ አሰፊ የተባሉ የካቡል ነዋሪ፤ የካርዛይን ተግባራት ሚዛናዊ በሆነ አመለካከት መመርመር ተገቢ ነው ይላሉ ።
«የካርዛይ ሥራዎች ሚዛናዊ በሆነ ዐይን ነው መታየት የሚኖርባቸው። የፕረስ ነጻነትና የሴቶች መብት ፤ እንዲሁም የመምረጥ መብት የተሻሻለው በእርሳቸው የሥልጣን ዘመን ነው። ይህ ትልቅ ርምጃ ነው። በሁለተኛው ዙር ምርጫ ካርዛይን አልመረጥኹም። የገቡትን ቃል አላከበሩምና! የጎሣ ጦር አበጋዞች እስካሁን የህዝብ እንደራሴዎች ተብለው በፓርላማ ይገኛሉ።»
ፕሬዚዳንት ሐሚድ ካርሳይ፤ አካራሪ እስላማዊ ተዋጊ ኃይሎችን ወንድሞቼ እያሉ በማባበል ለሰላም ውይይት እንዲቀርቡ ጥሪ ቢያስተላልፉም አልቀናቸውም።
ዋሂዳ ሹጃዪ የተባሉ በመዲናይቱ በካቡል የሚኖሩ ባለሱቅ ፣ አፍጋኒስታናውያን፤ ከታሊባኖች ውድቀት በኋላ ሚዛናዊ የሆነ ለዘብተኛ መሪ በማግኘታቸው ደስተኞች እንደነበሩና በኋላ የኤኮኖሚውና የፀጥታው ይዞታ አስተማማኝ ሊሆን እንዳልቻለ ገልጸዋል። ያም ሆኖ ፣ አሁንም ቢሆን የአፍጋኒስታን ዜጎች ዕድገትን አጥብቀው እንደሚሹ ነው የተናገሩት።
«የአፍጋኒስታን ተወላጆች፤ ታሊባኖች ከሥልጣን ከተወገዱ በኋላ አመዛዛኝ የሆኑ አዲስ ርእሰ ብሔር ለማግኘት በመብቃታቸው ደስተኞች እንደነበሩ የሚታወስ ነው። ነገር ግን ከጊዜ በኋላ፣ የፀጥታውና የምጣኔ ሀብቱ ይዞታ አሽቆለቆለ። በዛ ያሉ አፍጋኒስታናውያንም እንደገና መሰደድን ነበረ የመረጡት። መጀመሪያ ላይ ታሊባኖች በመወገዳቸው ህዝቡ ደስብሎት እንደነበረ አይታበልም። አሁንም አፍጋኒስታናውያን የሚሹት ትክክለኛ ዕድገትን ነው።»
በካቡል የፍሪድሪኽ ኤበርት ድርጅት የሥራ መሪ አድሪዬን ቮልተርስዶርፍ እንደሚሉት፣ ፕሬዚዳንት ሐሚድ ካርዛይ የአገራቸውን ሕዝብ መልሶ ለማዋኻድ የቱን ያህል ጠቃሚ ድርሻ እንዳበረከቱ ውሎ አድሮ ሳይመሠከርላቸው አይቀርም።
ተክሌ የኋላ
ሸዋዬ ለገሰ