አፍሪቃውያን እና የጀርመን ምርጫ
ዓርብ፣ መስከረም 3 2006የጀርመንን አመራር እና ፖሊሲ በቅርብ የተከታተሉ አፍሪቃውያን ፤ አንጌላ ሜርክል የስልጣን ጊዜያቸውን በሚገባ ተጠቅመዋል ባይ ናቸው። በተለይ በኮንትራት ሰራተኝነት ወደ ቀድሞ ምስራቅ ጀርመን የመጡ ሞዛምቢካውያን፤ ምስራቅ ጀርመን ላደጉት አንጌላ ሜርክል ይቆረቆራሉ። «ማድጀርመን» በመማል የሚታወቁት ወደ 15 ሺ የሚሆኑ ሞዛምቢካውያን እኢአ ከ 1979 ጀምሮ በቀድሞው GDR እንዲሰሩ ተፈቅዶላቸው ነበር፤ ይሁንና ምስራቅ ጀርመን ከምዕራብ ጀርመን ልትዋኃድ ስትል ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ ተደርገዋል። ታድያ ከነዚህ አንዱ የ47 ዓመቱ ነጋዴ አርናልዶ ሜንዴስ ናቸው።
« በሜርክል አስተዳደር ስር ጀርመን የአውሮፓን ኢኮኖሚው ቁንጮ ሆና እየመራች ትገኛለች። የዓለም አቀፉ የፋይናንስ ቀውስ እንኳን ብዙ አደጋ አላስከተለባትም። መምረጥ የምችል ቢሆን ኖሮ ለሜርክል ድምፄን እሰጥ ነበር»
ሌሎች የጀርመንን ፖለቲካ በቅርብ የሚያጤኑ « ማድጀርመንስ» እንዲሁ ሜርክልን ያደንቃሉ። ጀስቲን ሙትሴ የ 53 ዓመት ኤሌክትሪሺያን ናቸው። የሜርክል ስም ሲነሳ ትዝ የሚላቸው።«የቁጠባ ፖሊሳቸው ትዝ ይለኛል።እንደ ግሪክ ፖርቹጋል እና የመሳሰሉት ሀገሮች» የዶይቸ ቬለ ወኪሎች የሰበሰቡት አስተያየት እንደሚያመላክተው ሌሎች አፍሪቃውያንም የሜርክልን ምጣኔ ሀብታዊ ፖለቲካ ይከታተላሉ።
የኢኮኖሚ ትኩረት
የ 29 ዓመቱ ጃሬድ አምባ ጀርመን በኢኮኖሚ የደከሙ ሌሎች የአውሮፓ አባል ሀገራትን የምትረዳ ሀገር ናት፤ ሜርክል ኢኮኖሚው ከባድ በነበረበት ጊዜም እንዴት እንደሚመራ ያውቁበታል ይላሉ ኬንያዊው «ከቀድሞ እንደ ሄልሞት ኮል ካሉ ሌሎች መሪዎች ጋ ሜርክል ሲነፃፀሩ ጀርመን ላይ ባውዛ ያበሩባት ሰው እሳቸው ናቸው። ኢኮኖሚውን ብንመለከት ጥሩ እየተንቀሳቀሰ ነው። በአውሮፓ ህብረት የኢኮኖሚ ቀውስ የገጠማቸውን ሀገራት ድጋፍ በመስጠት ላይ ያለችው ሀገር በአሁን ሰዓት ጀርመን ናት። »
ምቩሜ ሎውሊ ፤ እሳቸውም ከኬንያ ናቸው፤ ሜርክል የዮሮ ቀውሱን ጫና ከጀርመን ላይ ለማውረድ ሞክረዋል ሲሉ ያክላሉ። « የኢነርጂውም ይሁን የኢኮኖሚ ፖሊሲያቸው የሚያስገርም ነው። የውጭ ፖሊሲውን የተመለከትን እንደሆነ ግን ይህን ያህል አይደለም። ጌርት ሽሮደርን ብንመለከት ብዙ ይጓዙ እና በዓለም ላይ ስለሚከሰቱ ነገሮች ይገልፁ ነበር። ሜርክል ግን ጀርመን የአውሮፓ የኢኮኖሚ ኃይል ሆና እንድትቆይ ብቻ ነው የሚጥሩት። እንደ እኔ ከሆነ የአውሮፓን ኢኮኖሚ መርተው ለመያዝ ነው የሚፈልጉት። እና ለራሳቸው ኢኮኖሚ እና ለዝህባቸው ስራ መፍጠር ላይ ነው ያተኮሩት።»
ኮትዲቫሪያዊው ጡረተኛ ኮፊ ፤ ሜርክል « ጠንካራ ሴት ናቸው» ሲሉ። ሃመድ ደግሞ የሜርክልን ስም ሲሰሙ አመራር እና በአውሮፓ አንድ ጠንካራ ሀገር ጀርመንን እንደሚያስታሳቸው ይገልፃሉ።
የጀርመን የአፍሪቃ ፖሊሲ
ይሁንና ሜርክል በአፍሪቃውያን ዘንድ ውዳሴ ብቻ ሳይሆን ትችትም ገጥሟቸዋል። ሜርክል በአፍሪቃ ስማቸውን እንዲወሳ የሚያደርግ ጭራሽ ምንም አይነት ስራ አልሰሩም ይላሉ የሬዲዮ አስተናጋጁ ዣን ባብቲስ ኮዲኦ« ለኔ የሚወክሉት ምንም ነገር የለም። የጀርመን መሪ ናቸው ፤ በቃ አለቀ»ሜርክል ጀርመን በዓለም አቀፍ ደረጃ ትልቅ ሚና ለማድረግ ሞክረዋል ይላሉ፣ ቻቻ ንያጎቲ ቻቻ ። በካቶሊካውያን ዮንቨርስቲ ውስጥ በሚገኘው የናይሮቢ አካባቢያዊ ልማት ተቋም ፕሮፌሰር ናቸው። « ለምሳሌ አፍሪቃን ብንመለከት የጀርመን መንግስት አቋም ይህ ነው ብዬ ለማለት ይከብደኛል።» በጀርመን የሚኖሩ ኢትዮጵያዊ ደግሞ የጀርመን የአፍሪቃ ፖሊሲ ይበልጥ በጀርመን ጥቅም ላይ ያተኮረ መሆኑን ይናገራሉ፤ እንደ የናይሮቢ ጋዜጠኛ ኔሊ ሞራ ከሆነ የሜርኩል ትኩረት በአውሮፓ ህብረት ላይ ብቻ ነው።
« ፖሊሳቸው በርግጥ ለአፍሪቃ ያን ያህል ትኩረት የሚሰጥ አይደለም። ብዙ ትኩረታቸው አውሮፓ ህብረት ላይ ነው። በድህነት ስንማቅቅ ከማየት። ይህ ትኩረት ለኛም ሊሰጥ ይገባል። ለልማት የሚበጅ ርዳታ ሲያስፈልገን መሰናክል ከማበጀት በቶሎ ቢረዱን ይሻላል። ለምሳሌ ዲሞክራሲ እና ጥሩ የመንግስት አመራር በቅድሚያ ካላሳያችሁ ርዳታ አታገኙም የሚሉትን ማለቴ ነው።»
ሌሎች እንደ ጀምስ ሞባት ያሉ ኬንያውያን ደግሞ አንጌላ ሜርክል በጀርመን መህራይተ መሪ ለመሆን የቻሉ ብቸኛ ሰው ናቸው እያሉ ያደንቋቸዋል።« ከ2 ዓመታት በፊት ኬንያን ጎብኝተው ነበር። አዲሱ መንግስታችን ለማህበራዊ ኑሮ ማሻሻያ በተግባር ላይ እንዲያውሉ 140 ሚሊዮን ዩሮ ርዳታ ቃል ገብተዋል። ለዚህ ደግሞ እናመሰግናለን። እና እንደ ጀርመን መራኂተ መንግሥት ጥሩ ስራ እየሰሩ ያሉ ይመስለኛል።» የሶሻል ዲሞክራቲ ፓርቲ አባል እና የጀርመን ርዕሰ ብሄር እጩ ከሜርክል ጋ ሲነፃፀሩ ብዙም አይታወቁም።
«ሽታይን ብሩክ እ… የተቃዋሚው ፓርቲ እጩ ! ያውቃሉ የጀርመን ፖለቲካ ብዙም አያሳስበኝም። ከዚያ ይልቅ እዚህ ሞዛምቢክ የሚከሰተውን ነው የምከታተለው።» ይላሉ በማፑቶ የሚኖሩት ኤሚላ ዱቫኔ።
ልደት አበበ
ነጋሽ መሐመድ