አዲሷ የጀርመን የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽነር
ዓርብ፣ የካቲት 18 2008ለሁለት ዓመታት በዚህ ኃላፊነት የቆዩት ሶሻል ዴሞክራቱ ሽትሬሰር ሳይታሰብ በፈቃዳቸዉ ሥራቸዉን የለቀቁት በግል በዛብኝ ባሉት የሥራ ጫና እና ሀገሪቱ ልታጠብቅ ያቀደችዉ የስደተኞች ሕግ ከግል አመለካከቴ ጋር አይሄድም ብለዉ ነዉ። በቦታቸዉ የተተኩት አዲሷ ተሿሚም የሶሻል ዴሞክራት አባል እና የባየርን ፌደራላዊ ግዛት ምክር ቤት አባል ናቸዉ።
አዲሷ የጀርመን የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽነር የ48ዓመቷ ቤይርብል ኮፍለር የልማት ፖለቲካ ላይ የሚያተኩሩ እና ከጎርጎሪዮሳዊዉ 2013ዓ,ም ጀምሮ የምክር ቤት የዘርፉ ቃል አቀባይ ሆነዉ ሠርተዋል። የጀርመን የዜና አዉታር እንደሚለዉ ኮፍለር ይህን ዝንባሌያቸዉን አሁን በተሾሙበት መሥሪያ ቤት ሥራ ላይ ሊያዉሉት ይችላሉ።
«እዚህ ብዙም የማይነገር በበርካታ የአፍርቃ ሃገራት ቁጥራቸዉ እጅግ የበዛ ሰዎች በስደተኛ መጠለያ ዉስጥ እጅግ በጣም ባስቸጋሪ ሁኔታ ይኖራሉ። ትኩረታችንን ወደእነዚህ ሰዎችና አካባቢዎች ማድረግ እና አኗኗራቸዉ እንዲሻሻልም አስተዋፅኦ ማድረግ እንደሚያስፈልግ አስባለሁ።»
እንዲያም ሆኖ እሳቸዉ የተኳቸዉ ክርስቶፍ ሽትሬሰር የተቃወሙትን የጀርመን ምክር ቤት ድምጽ የሚሰጥበትን ጠንካራዉን የስደተኛ ሕግ አላጣጣሉም። የመንግሥት ተጣማሪ ፓርቲዎች ካንድ መግባቢያ ላይ ደርሰዋል፤ ኮፍለርም ይህ እንዴት በመንግሥት አስተዳደር ሥራ ላይ እንደሚዉል መከታተሉ ጠቃሚ ነዉ የሚል አቋም አላቸዉ።
ሁለተኛዉ የስደተኞች ጉዳይ ሰነድ የሚባለዉ ጥገኝነት ጠያቂዎች ጉዳያቸዉ በቶሎ እንዲታይ እና ዝቅተኛ ከለላ የሚሰጣቸዉ ጥገኝነት ጠያቂዎችም ቤተሰቦቻቸዉን ወደጀርመን እንዳያስመጡ ያግዳል። ሶሻል ዴሞክራት ፓርቲ በበኩሉ ወጣት ጥገኝነት ጠያቂዎች ከወላጆቻቸዉ ጋርም ሆነ ከወንድም እህቶቻቸዉ ጋር ይህን እንድል እንዲያገኙ ይጠይቃል። ኮፍለርም በግላቸዉ እንዲህ ላለዉ «ደግነት» ይሟገታሉሉ።
«ዋና ትኩረቴ የሰብዓዊ መብት በትክክል እንዲከበር ነዉ። ይህም የሴቶች እና የልጆችን መብቶች ጨምሮ በሥራ ቦታ ሁሉም የሰዉ ልጅ መብቶች እንዲከበሩ ነዉ። በዚያም ላይ ለምሳሌ ከባርነት ነፃ የመዉጣት ትግልን እንደማንኛዉም የሰዉ ልጅ መብት፤ ከተለያዩ አስቸጋሪ ነገሮች ሽሽትን ሁሉ ያካትታል።»
የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ጽሕፈት ቤቱ በጀርመን የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ዉስጥ ነዉ። ከዋና ተግባራቱ አንዱ የጀርመን የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የሚያቀርባቸዉ ፖሊሲዎች ከሰብዓዊ መብቶች እና ሰብዓዊ ርዳታዎች ጋር መጣጣማቸዉን መመዘን ነዉ። በጀርመን ዉስጥ የሚፈፀሙ የመብት ጥሰቶች ቢኖሩ ግን በዚህ ኮሚሽን ሳይሆን በሕገ መንግሥቱ መሠረት በፍርድ ቤት የሚታይ ነዉ የሚሆነዉ። ለዚህ እንደዉም ፊርማ አሰባስቦ ለእንባ ጠባቂ የሚያቀርብ ኮሚቴም አለ። የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ፍራንክ ቫልተር ሽታይን ማየር አዲሲቷ የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽነርን በተመለከተ እማኝነታቸዉን እንዲህ ሰጥተዋል።
«ቤርብል ኮፍለርን የህይወት ታሪክ የተመለከተ፤ ቤርብል ኮፍለር ከህይወት ጋር የተፋለሙ ወይዘሮ መሆናቸዉን፤ አስቸጋሪ ሁኔታዎችንም መወጣት የቻሉ እንደሆኑ ይረዳል። እናም በዚህ ሰዓት በርካታ ኃላፊነቶች ወደሚጠይቀዉ አዲስ የሥራ ኃላፊነት ለመምጣት በመወሰናቸዉ ተደስቻለሁ።
በሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽኑ ዉስጥ ከክላዉዲያ ሮዝ ቀጥሎ ቤርብል ኮፍለር ሁለተኛዋ ሴት ባለስልጣን መሆናቸዉ ነዉ። ሩሲያኛ እና ስፓኒሽኛ ያጠኑት የቋንቋ ምሁር የጀርመን የትምህርት ልዉዉጥ ተቋም ዉስጥ በቋንቋ መምህርትነት እና የዩኒቨርሲቲ አስተማሪነትም ሠርተዋል። በሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ዉስጥ የባለስልጣን ለዉጥ የተደረገዉ ጀርመን የስደተኞች ቀዉስ እና የሰብዓዊነት ጉዳይ ችግር በገጠማት ወቅት ነዉ። በጀርመን የአምነስቲ ኢንተርናሽናል ዋና ፀሐፊ ስሊም ካሊስካን የስደተኞችን ቁጥር ለመቀነስ በሚደረገዉ ሂደት የሰብዓዊ መብቶች ጉዳይ ትኩረት እንዳያጣ ስጋታቸዉን ገልጸዋል።
በርን ግሬዝለር / ሸዋዬ ለገሠ
አዜብ ታደሰ