አዲስ የተረቀቀው የመገናኛ ብዙሃን አዋጅ
ቅዳሜ፣ ሰኔ 15 2011አዲስ የተረቀቀው የመገናኛ ብዙሃን አዋጅ የመገናኛ ብዙሃንና የመረጃ ነጻነት እንዲሁም የብሮድካስት አዋጁን የሚሽር እና የሃገሪቱን የፖለቲካ የዴሞክራሲ እና የቴክኖሎጅ እድገት ታሳቢ ተደርጎ በሁለቱ አዋጆች የነበሩ ችግሮችንም የሚፈታ እንደሚሆን ተነግሯል።ረቂቁ የኢትዮጵያ የመገናኛ ብዙሃን ባለስልጣን የሚባል ራሱን የቻለ ተጠሪነቱም ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሆነመስሪያ ቤት ያቋቁማል።
ከዚህ በፊት ይቆጣጠርና ይከታተል የነበረውን የብሮድካት መገናኛዎችን ጨምሮ የህትመት መገናኛዎችንም የሚመራ ነው ተብሏል። አዋጁ የውጭ ዜጎች እስከ 25 በመቶ ድርሻ እንዲሳተፉ የሚፈቅድ ሲሆን ፤ ስም ማጥፋት በሚል በመገናኛ ብዙሃንና በጋዜጠኞች ላይ ይቀርብ የነበረውን የወንጀል ተጠያቂነት በማስቀረት በፍትሃብሄር ብቻ እንዲታይ አድርጎ ደንግጓል።ያም ሆኖ ግን ከዚሁ ጋር በተያያዘ የቅጣት ጣራውን ከ 100 ሽህ ወደ 300 ሽህ ብር ከፍ አድርጎታል። በረቂቁ ዙሪያ በተደረገው ውይይት ባለ ስልጣኑ የመድብለ ፖርቲ ውክልና እና መልክ ለሌለው ፖርላማ ተጠሪ መሆኑ ተገቢ አይደለም የሚል ጥያቄ አስነስቷል። ለብዙ ጋዜጠኞች እስር እና እንግልት ምክንያት ነበር የተባለው አዋጅ ቁጥር 590 / 2000 በሂደት የሚሻሻል በመሆኑ ይስተዋሉ የነበሩ ችግሮች እንደሚቀረፉ 72 ገጽ ባለው ረቂቅ አዋጅ ተመላክቷል።
ሰለሞን ሙጬ
ልደት አበበ