1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አዲስ አበባ በራስታዎች ዳንኪራ ደመቀች

ሰኞ፣ መስከረም 13 2000

ከምድረ ጃማይካና ከመላው ዓለም የተሰባሰቡ ቁጥራቸው ወደ 30 ሺህ የሚጠጉ ራስታዎች ለሙዚቃው ድግስ ኢትዮጵያ መግባታቸው ታውቓል።

https://p.dw.com/p/E0gm
የሬጌው ንጉስ
የሬጌው ንጉስ

ራስ ተፈሪ፤ራስታ
ራስታ ቃሉ ራስ-ተፈሪ መኮንን ከሚለው፤ማለትም ዓፄ ኋይለስላሴ ከንግስና በፊት ቀድመው ይጠሩበት ከነበረው ስማቸው የተወረሰ ነው።

የራስታ አለያም የራስ-ተፈሪያዊነት እንቅስቃሴ ማሕፀነ-ምድር ጭምርም ናት ኢትዮጵያ።እጅግ እምቅ የሆነ የበርካታ ባህል ደሴትነቷ ደግሞ ይህችን ጥንታዊት አገራችንን ሁሌም ልዩ ያደርጋታል። እናም ከመላው ዓለም ሁሉ ልዩ በሆነው የቀን አቆጣጠር ቀመሯ ተመርታም ሶስተኛውን ዓመዐት አለያም ሚሌኒየም ከቅርብ ቀናት በፊት ተቀላቅላለች።

ዓመዐቱ በተለያዩ ዝግጅቶች እየተከበረ ዓመቱን በሙሉ የሚዘልቅ ሲሆን፤ስፍር ቁጥር የሌለው ራስታ ቅዳሜ መስከረም11 እና12 በመስቀል አደባባይ መገኘቱም በዚሁ ምክንያት ነው ሲል አዧንስ ፍራንስ ፕሬስ አትቷል።በሙዚቃ ድግሱ ታዋቂዎቹ ኪንግ ኮንግ እና ሉቺያኖን ጨምሮ የተለያዩ አቀንቃኞች በመገኘት ታዳሚውን ሲያዝናኑም ውለዋል።የዛሬ 2 ዓመት የሬጌው ንጉስ ቦብ ማርሌይ 60ኛ ዓመት ሲከበር በዚሁ የመስቀል አደባባይ እንደነበር የሚታወስ ነው።

የቦብ ማርሌይ ሙዚቃዎችን ወደአማርኛ የተረጎማቸውና የዝግጅቱ ተባባሪ አዘጋጅ የሆነው ራስ አቢይ ጥላሁን በበኩሉ፤ኢትዮጵያ ፈፅሞ በቅኝ አልተገዛችም፣የራሷ የሆነ ቤተክርስቲያን አላት፣የአፍሪካም ዳግም ትንሳኤ ተምሳሌት ናት፣እኛ ግንባር ቀደምች ነን፤እናም ይህ የተስፋ ምልክት ነው ሲል የዝግጅቱን ልዩ መሆን ገልጿል።

እንደ ሙዚቃ ድግሱ አዘጋጅ ራስ ኬሽ ካሳዬ ገለጻ ደግሞ፤ በሁለቱ ቀናት የሙዚቃ ዝግጅት ወደ ሃያ አምስት የሚጠጉ አቀንቃኞች ተሳትፈዋል።ይህ የሙዚቃ ድግስ ለአንድ ዓመት የሚዘልቀው የኢትዮጵያ ዓመዐት አንዱ አካል እንደሆነም ለማወቅ ተችሏል።