አደገኛው የሜድትራኒያን ባህር ጉዞና ኢትዮጵያውያን
ሐሙስ፣ ሚያዝያ 8 2007ከባለቤቱ ጋር ከሊቢያ የትሪፖሊ ወደብ በመነሳት በጀልባ የሜድትራኒያን ባህርን ለማቋረጥ የተዘጋጀው ሰለሞን መንግስቴ «ምናልባት አደጋ ከተከሰተና ወደ ባህር ከወደቀ የተወሰነ የመንሳፈፍ እድል ካለው የነፍስ አዳኞቹ ለመያዝ እንዲመቻቸው የምትለብሱት ጃኬት በርቀት ሊታይ የሚችል ቀይ ወይም ነጭ ቀለም ያለው ይሁን» የሚል ምክር ተሰጥቶታል።የጉዞ መስመሩ ሞትና መከራ ቢበረክትበትም ሰለሞን እና ባለቤቱ የዝና በሚቀጥለው እሁድ ጉዞ ይጀምራሉ።
ከአምስት መቶ በላይ ስደተኞች ጭና ወደ ጣሊያን ትጓዝ ከነበረችው መርከብ ተሳፋሪዎች መካከል ከአራት መቶ በላይ የሚሆኑት ባለፈው እሁድ ሳይሰምጡ እንዳልቀረ ተሰምቷል። የጣሊያን የባህር ዳር ጠባቂዎች በመርከቧ ከተሳፈሩት ስደተኞች መካከል 144ቱን ማዳን የቻሉ ሲሆን የቀሪዎቹን መጨረሻ ለማወቅ በአየርና በባህር ፍለጋ ላይ መሆናቸውን አስታውቀዋል። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ጉዳይ ተመልካች መስሪያ ቤት ከፍተኛ ቃል አቀባይ ዊሊያም ስፒንድለር ከአራት መቶ በላይ የሆኑት ስደተኞች መሞት ከተረጋገጠ በዚህ አመት ብቻ በተመሳሳይ አደጋ የሞቱት ሰዎች ቁጥር 900 ይደርሳል ሲሉ ለዶይቼ ቨሌ ተናግረዋል።
መኳንንት ከሊቢያ የወደብ ከተማ በመነሳት ወደ አውሮጳ ለመጓዝ የተዘጋጀ ኢትዮጵያዊ ነው። ባለፈው ሳምንት ጉዞ ጀምሮ የነበረው መኳንንት እሱ የተሳፈረባት ጀልባ በመበላሸቷ መመለሱን ይናገራል።
«ትንሽ ነች። ካፒቴኑ 75 ሰው ነበር ጫኑልኝ ብሎ የነበረው። ከመጠን በላይ ጫኑባት ወዲያውኑ ተበላሸች።» የሚለው መኳንንት ጊዜውን ይጠብቃል እንጂ መጓዙ እንደማይቀር እርግጠኛ ነው።
ከሊቢያ ወደ የመን በባህር ላይ የሚጓዙት አነስተኛ ጀልባዎች ለጉዞው የሚመጥኑ አለመሆናቸው ይነገራል። ከአቅማቸው በላይ የሚጭኑት ጀልባዎች ችግር ሲገጥማቸው አሊያም የአየር ሁኔታው ሲከብድ ለእርዳታ የሚደርሱት የእርዳታ ድርጅቶችና የጣሊያን ድንበር ጠባቂዎች ተጨማሪ ችግር ገጥሟቸውል። ስደተኞችን ለመታደግ ጥረት በሚደረግበት ወቅት ህገ-ወጥ የሰዎች አዘዋዋሪዎች ጥይት መተኮሳቸው ተሰምቷል። አንድ ጊዜ ሞክሮ በጀልባ መበላሸት ምክንያት ሳይጓዝ የቀረው መኳንንት አሁንምአደጋ ከደረሰበት ጀልባ በተጨማሪ ሌሎች ሶስት አብረው ሳይጓዙ እንዳልቀረ ይናገራል።
አሁን አደጋ በገጠማት መርከብ ላይ የከተሳፈሩትና ከዳኑት መካከል አብዛኞቹ ህጻናትና አዳጊ ወጣቶች መሆናቸውን ህጻናት አድን ድርጅት የጣሊያን ቢሮ አስታውቋል። ድርጅቱ በዚህ አደገኛ መንገድ ወደ አውሮጳ ለመግባት የሚጓዙ ወጣቶች ቁጥር ሊጨምር ይችላል ሲልም አስጠንቅቋል። ጣሊያን በሜድትራንያን ባህር የሚመጡትን ስደተኞች ለመታደግ የአውሮጳ ህብረት ትብብር እንዲያደርግ መጠየቋን አዣንስ ፍራንስ ፕሬስ የዜና ወኪል ዘግቧል። ሰለሞን ከሊቢያ ወደ ጣሊያን ጉዞ የሚጀምረው ብቻውን አይደለም። ሁለት ህጻናትን ጨምሮ በርካታ ሴቶችም ወደ አውሮጳ ታደርሰናለች ብለው ተስፋ የጣሉባትን መርከብ በመጠባበቅ ላይ ናቸው።
የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ኮሚሽንን ጨምሮ በርካታ የእርዳታ ድርጅቶች በባህር ላይ በአደገኛ ሁኔታ ወደ አውሮጳ ለመሻገር የሚሞክሩ ስደተኞችን ለመታደግ የአውሮጳ አገራት እንዲተባበሩ ጥያቄ በማቅረብ ላይ ናቸው። ካለፈው አርብ ጀምሮ ከ8,000 በላይ ስደተኞች መታደግ የተቻለ ሲሆን የአካባቢው የአየር ሁኔታ ለውጥ በማሳየቱ ወደ አውሮጳ ለመሻገር የሚሞክሩ ሰዎች ቁጥር ያድጋል የሚል ስጋት አይሏል።
እሸቴ በቀለ
አርያም ተክሌ