አውሮጳና ፀረ የባህር ላይ ወንበዴዎች
ሰኞ፣ መጋቢት 17 2004የአውሮፓ ህብረት በሶማሊያ የባሕር ላይ ወንበዴዎችአንጻር በጀመረው ትግሉ በባህሩ ብቻ ሳይሆን በየብስም የባሕር ወንበዴዎችንና መሳሪያቸዉን ለመምታት መወሰኑን አስታወቀ።
የውሳኔው መነሻ ፤ ምንም እንኳን የህብረቱ ጦር መርከቦች ተልዕኮ የባህር ላይ ወንበዴዎችን ተግባር ቢያሰናክልም ፤ ወንበዴዎቹ ዘረፋቸውን ባለማቋረጣቸው ነው ህብረቱ ይህን ውሳኔ የወሰደው። ይኸው የአውሮጳ ህብረት ውሳኔ ጀርመን ውስጥ እምብዛም ድጋፍ አላገኘም።
ባለፈው አመት ብቻ በ 237 መርከቦች ላይ የሶማሊያ የባህር ላይ ወንበዴዎች ጥቃት ማድረሳቸውን ለንደን የሚገኘው አለም አቀፍ የባህርጉዞ ቢሮ በምህፃሩ IMB አስታውቋል። በአሁኑ ሰዓት 13 መርከቦች እና 197 የታገቱ ሰዎች በሶማሊያ የባህር ላይ ወንበዴዎች ቁጥጥር ሥር ይገኛሉ።
እአአ ከ2007 ጀምሮ የባህር ላይ ወንበዴዎች ጥቃት በ10 እጥፍ ጨምሯል። በዚህም የተነሳ የአውሮጳ ኅብረት ባለፈው ዓርብ እንዳስታወቀው፣ ወደፊት በባህሩ ብቻ ሳይሆን በመሬትም ያሉ የወንበዴዎቹን ምሽጎች ያጠቃል። የጀርመን ፌዴራዊ ምክር ቤት የአውሮጳ ህብረት በሶማልያ ባህር የጀመረውን ተልዕኮ ለማስፋፋት ስለወሰደው ውሳኔ ድምጽ ይሰጥበታል። ውሳኔው በጀርመን ገዢውን ጥምር መንግሥትና የተቃዋሚ ፓርቲዎችንም እያከራከረ ይገኛል። በምክር ቤቱ የአረንጓዴው ፓርቲ የመከላከያ ጉዳይ ቃል አቀባይ- ኦሚድ ኖሪፖር ፓርቲያቸው ውሳኔውን ሊደግፍ እንደሚችል ቢገልጹም፣ ጉዳዩን በጥንቃቄ እንደሚመለከቱ አስታውቀዋል።
«በመጀመሪያ የተሰጠው ስልጣን እስከ ምን ድረስ እንደሆነ እንመረምራለን። ከዛም በኋላ እንወስናለን። ዝርዝሩን ሳንመለከት አስቀድመን ምንም ነገር አናደርግም። እርግጥ ልንለው የምንችለው፤ ተልዕኮውን ለማስፋፋት የተደረሰውን እቅድ እጅግ በጥንቃቄ እንደምንመለከተው ነው። ወደፊት ተግባራዊ ይሆናል የተባለው ዕቅድ ግልጽ አይደለም።»
በዛ ላይ የባህር ላይ ወንበደዎቹ በፍጥነት ስልታቸውን ሊቀይሩ እና የተያዘው እቅድ መልሶ ውድቅ ሊሆን እንደሚች ኖሪፖር ስጋታቸውን ገልፀዋል።
በርግጥ የአውሮፓ ህብረት በምን አይነት መንገድ የባህር ላይ ወንበዴዎቹን በየብስ ሊታገል እንዳቀደ ያወጣው ዝርዝር የለም። ወሳኙ ዝርዝሩ አለመሆኑን የገለጹት የሶሻል ዴሞክራቱ ፓርቲ (SPD) የመከላከያ ጉዳይ ባለሙያ ራይነር የባህር ላይ ወንበዴዎቹን ዒላማዎች በአየር ኃይል በማጥቃቱ ርምጃ ወቅት ንፁሀን ሊገደሉ የሚችሉበት ስጋት መኖሩን ነው የገለጹት፥ እና ፓርቲያቸው እቅዱን እንዳይደግፍ ያማክራሉ። በአሁኑ ሰዓት ወደ 18 000 የሚጠጉ የአፍሪቃ ህብረት ሰላም አስከባሪ ወታደሮች በሶማሊያ ቢሰማሩም፣ እስካሁን በአገሪቷ የተረጋጋ ሁኔታ አይታይም።
ሶማሊያውያኑ የባህር ላይ ወንበዴዎች በዓለም አቀፍ የንግድ መርክቦች ላይ የሚያደርሱት ጥቃት ያለማቋረጥ ይጨምር እንጂ መርከቦችን ሙሉ በሙሉ በቁጥጥር ስር የማዋሉ ሁኔታ ቀንሷል። ይህም የሆነበት ምክንያት የዓለም አቀፍ የንግድ መርከቦች የበለጠ ተደራጅተው እና የታጠቁ የደህንነት ሰዎችን አሳፍረው ስለሚጓዙ እንደሆነ IMB ገልጿል። በአደን ባህረ ሰላጤ ብቻ በአመት 30 000 የሚደርሱ የንግድ መርክቦች ይጓዛሉ። የነዚህን መርከቦች ደህንነት ለመከላከል ወደ አስር የሚጠጉ የአውሮጳ ህብረት የአታላንታ ተልእኮ መርከቦች በስፍራው ይገኛሉ። የአውሮፓ ህብረት የባህር ላይ ውንብድና አጠናክሮ በየብስ ላይ ለመዋጋት በማሰብ የወጠነውን እቅድ በቦን ዮንቨርሲቲ የአፍሪቃ ቀንድ የፖለቲካ ተንታኝ- ኮንራድ ሼተር አይደግፉትም።
ይህ የአረንጓዴው እና የሶሻል ዴሞክራቶቹ ፓርቲዎች የመከላከያ ጉዳይ ቃል አቀባዮች - ኦሚድ ኖሪፖር እና ራይነር አርኖልድ የሚጋሩት ሀሳብ ነው። የአውሮጳ ህብረት ተልዕኮ መስፋፋትን በተለይ የቦን ዮንቨርሲቲ የአፍሪቃ ቀንድ የፖለቲካ ተንታኝ- ኮንራድ ሼተር እንደ ችግር የሚያዩበት ሌላኛው ምክንያት በአንድ በኩል ለዲሞክራሲ እና ለሰብዓዊ መብት በቆሙት፣ በሌላ በኩል ደግሞ ምንም አይነት እድል ባላገኙ ሰዎች ላይ የበለጠ የሀይል ርምጃ ለሚወስዱት ምዕራባውያት አገሮች የሞራል ጥያቄ ማስነሳቱን ነው።
ልደት አበበ
አርያም ተክሌ