አከራካሪው የዘረ-መል ለውጥ
ዓርብ፣ ነሐሴ 23 2006እንደተባለው አገር በቀል የሆኑ አዝርእትን፤ አትክልቶችን ፣ ፍርፍሬዎችን ጥራትና ምርታማነት ከፍ ማድረግ የሚቻልበት ዝግመታዊ ለውጥ መሰል ከሳይንስ ያልተለዬ መላ ቢኖርም፣ በቀጥታ በሥነ-ቴክኒክ አጠቃቀም የአዝርእትም ሆነ የእንስሳት የተፈጥሮ ባሕርያት እንዲለወጡ ማድረግ የሚቻልበት አሠራር፣ ከአንዳንድ ተቋማት ላቅ ያለ የማደፋፈሪያ ምክር የሚሰጥበት ውትወታ የሚደረግበት ሁኔታ መሥፋፋቱ አልቀረም።
የአየር ፤ የአፈር የውሃና የአካባቢ ይዞታ ወሳኝነት ያላቸው ሲሆን በቀጥታ ነባቤ-ቃልን ተጠቅሞ የትም ቦታ በግብርና ቀመስ የአዝርእትን የሥነ ሐይወት ዕውቀት፣ የአዝርእትን የአትክልቶችን ፍራፍሬዎችንና እንስሳትን የተፈጥሮ የዘር ባህርይ እንዲለወጥ ግፊት ማድረግ ምንጊዜም በጎ ሐሳብ የሠነቀ ነው ብሎ መቀበል እንደማይቻል ፣ እንዲያውም አጠራጣሪ መሆኑን ነው ባለፈው ሳምንት ያነጋገርናቸው ዶ/ር መላኩ ወረደ ያስረዱን። አንድ ርምጃ ሲወሰድ የሚያስከትለው ጉዳት ምን ሊሆን እንደሚችል ታሳቢ አድርጎ መንቀሳቀስ እንደሚገባ ራሳቸው ከታዘቡት አንድ ታሪክ በመነሣት እንዲህ ይላሉ።
ለዚህ ዝግጅት መነሻ የሆነን ባለፈው ሳምንት እንደጠቀስነው፣ በሜክሲኮ 300,000 ያህል ከአነዚህም ገሚሱ አነስተኛ የመሬት ይዞታ ያላቸው ባቄላ አምራቾች ያነሱት ጥያቄ ነው። እንደምሳሌም ፣ከአንድ ሄክታር መሬት በቶን የሚመረተው አገር በቀል ባቄላና የተፈጥሮ ባሕርዩ የተለወጠ በቆሎ ምርት መጠን ያን ያህል ልዩነት አለማሳየቱ የተጠቀሰበት ሁኔታ ነው። በፖላንድ፤ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ብቻ በመጠቀም የሚያመርቱ አርሶ አደሮች ቁጥር ባፋጣኝ በመጨመር ላይ መሆኑ ይነገራል። በዚህ ረገድ ከ 1,8 ሚሊዮኑ አርሶ አደሮች መካከል 26,000 ው ለተፈጥሮ አካባቢ፣ ለሰውና እንስሳም ክብካቤ በማድረግ የተሠማሩ መሆናቸውን የሚገልጽ የምሥክር ወረቀት ያገኙ ናቸው።
ስለግብርና ቀመስ የሥነ ሕይወት ዕውቀት(አግሪካልቸራል ባዮቴክኖሎጂ) ምርምር አያሻም አይባልም፣ የመጨረሻው ግብዓት፣ ምን ሊሆን፣ ምን ሊያስከትል እንደሚችል ገና ተጣርቶ ባልታወቀበት ሁኔታ፣ የሚመራመሩ ፤ የሚከራከሩ ለወገንም ጥቅም የሚያስቡ ኢትዮጵያውያን ሳይንቲስቶች እንዲሁ ከውጭ ለሚቀርብ ግፊትም ሆነ ውትወታ የላቀ ግምት ይሰጣሉ ብሎ ማሰብ ይከብዳል። ካለፈዉ የቀጠለዉን የባለሙያ ማብራሪያ ከድምፅ ዘገባዉ ያድምጡ።
ተክሌ የኋላ
ነጋሽ መሐመድ